የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ልዩ ዘገባ

ፋብሪካው ከነገ ጀምሮ ስኳር የማምረት ሥራውን ይጀምራል

Dec 2, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

አዲስ አበባ፤ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፡-የክረምት ወቅት ጥገና ሲደረግለት የሰነበተው ወንጂ ስኳር ፋብሪካ ከነገ ሕዳር 22 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ሸንኮራ አገዳ በመፍጨት ስኳር የማምረት ሥራውን ይጀምራል።

ሸንኮራ አገዳ ወደ ፋብሪካው የሚያጓጉዙ ማሽነሪዎች እና የፋብሪካው የጥገና ሥራ መጠናቀቁን የወንጂ ስኳር ፋብሪካ ዋና ሥራ አስኪያጅ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ እዩኤል ለላንጎ አረጋግጠዋል።

በሌላ በኩል ስኳር ለማምረት የሚያስችሉ ሸንኮራ አገዳዎች ዛሬ እንደተቆረጡ ለኢዜአ ገልጸዋል።


በዲዛይን ካፓሲቲው መሠረት የፋብሪካው በቀን ሸንኮራ አገዳ የመፍጨት ዐቅም 6 ሺህ 250 ቶን መሆኑን ገልጸው፥ ያለውን የሸንኮራ አገዳ አቅርቦትና ሌሎች ምክንያቶች ታሳቢ በማድረግ በቀን 4 ሺህ 890 ቶን ሸንኮራ አገዳ በመፍጨት ሥራውን ይቀጥላል ብለዋል።

በዓመት 601 ሺህ 574 ነጥብ 25 ቶን ሸንኮራ አገዳ በመፍጨት 70 ሺህ 239 ነጥብ 8 ቶን ስኳር እንደሚያመርትም አስገንዝበዋል።

ፋብሪካው በሙሉ ዐቅሙ ሸንኮራ አገዳ መፍጨት እንዲችል በአርሶ አደር ማሳ ተጨማሪ የሸንኮራ አገዳ ማሳ ለማልማት ዕቅድ ተይዞ እየተሠራ መሆኑንም አስታውቀዋል።

የሸንኮራ አገዳዎችን ዝርያ የማሻሻል፣ሸንኮራ አገዳ የመፍጨት፣ ስኳር የማምረት ዐቅምና የጨመቃ ሂደት ላይ ምርታማነትን የሚያሳድጉ ሥራዎች በጥገና ወቅት መከናወናቸውን ጠቅሰዋል።

ለዘንድሮው ስኳር የማምረት ሥራ በአማካይ 13 ነጥብ 9 በመቶ የስኳር ይዘት ያለው የሸንኮራ አገዳ ዝርያ ለፋብሪካው እንደሚቀርብም አመላክተዋል።

ፋብሪካው በበጋው ወቅት ሸንኮራ አገዳ በመፍጨት ስኳር የሚያመርት ሲሆን፤ በቀሪዎቹ ወራት በሚኖረው ዝናብና ተፈጥሯዊ ሁኔታ ስለማያመርት ጥገና እንደሚደረግለት ይታወቃል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.