የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ልዩ ዘገባ

የብዙኃን ትራንስፖርት ፍላጎትን ከማሟላት አኳያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው

Dec 8, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

አዲስ አበባ፤ ህዳር 25/2018(ኢዜአ)፦ የብዙኃን ትራንስፖርት ፍላጎትን ከማሟላት አኳያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በረኦ ሃሰን ገለጹ።

መንግስት በኤሌክትሪክ ኃይል የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን ለማስፋት ልዩ ትኩረት ሰጥቷል።

ሚኒስትር ዴኤታው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት መጠነኛ መቀመጫ ባላቸው ወንበሮች የትራንስፖርት ፍላጎት ማሟላት አዳጋች መሆኑን አንስተዋል።

በመሆኑም መንግስት አማራጭ የተሽከርካሪ አቅርቦትን በማስፋት የትራንስፖርት አገልግሎት ተደራሽነት ለማረጋገጥ እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል።


በኤሌክትሪክ ኃይል የሚሰሩ ተሽከርካሪዎች ያላቸው ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ የጎላ መሆኑን ጠቁመው፤ መንግስት በስፋት ወደ ሀገር ውስጥ እንዲገቡና አገልግሎት እንዲሰጡ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝም አመልክተዋል።

በተለይም በፖሊሲው የተካተተውን የብዙሃን ትራንስፖርት ፍላጎት ከማሟላት አኳያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

በዚህም የትራንስፖርት አገልግሎቱን በእጅጉ በማሳለጥ በየጊዜው እየጨመረ ላለው የብዙሃን ትራንስፖርት ፍላጎት ምላሽ እየሰጠ ስለመሆኑ ገልጸዋል።

በቅርቡ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተግባራዊ የተደረጉ 110 የብዙሃን ትራንስፖርት ማመላለሻ ''ቬሎሲቲዎች'' እጥረት ባሉባቸው 11 መስመሮች እንዲሰማሩ የተደረገ ሲሆን፤ በዚህም ከፍተኛ ለውጥ መጥቷል ብለዋል።

እንዲሁም 22 በኤሌክትሪክ የሚሰሩ ሚኒባሶች ከቬሎሲቲዎቹ ጋር ተጣጥመው አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉን ጠቅሰው፤ ይህም የትራንስፖርት ፍላጎትን ተደራሽ ለማድረግ ዓይነተኛ ሚና አለው ነው ያሉት።

እንዲሁም በኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የታክሲ አገልግሎት የሚሰጡ አደረጃጀቶች እየተፈጠሩ መሆኑ ጠቁመው፤ ለዚህም ከግሉ ዘርፍ ጋር በመተባበር የትራንስፖርት አገልግሎቱን ተደራሽ የማድረግ ሂደት እንዳለ አብራርተዋል።


ኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ተግባራዊ ማድረግ ከጀመረችበት ጊዜ አኳያ አሁን የደረሰችበት ደረጃ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን ከፍ ያደርገዋልም ብለዋል።

በተለይም የግለሰብ ተሽከርካሪዎችን ጨምሮ የብዙሃን ትራንስፖርትን ወደ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ማስገባት መጀመሩ ትልቅ እምርታ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው ገልጸዋል።

ይህም ዘርፉ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት ያለው ፋይዳ እንዲጨምር በማድረግ በኩል ጉልህ አስተዋጽኦ አበርክቷል ነው ያሉት።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.