የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ልዩ ዘገባ

በምስራቅ ሸዋ ዞን የሚገኙ ማእድናትን በጥናት በመለየት ኢኮኖሚያዊ ፋይዳቸውን ለማሳደግ በቅንጅት እየተሰራ ነው

Dec 11, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

አዳማ፤ ታህሳስ 2 / 2018 (ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የሚገኙ ማእድናትን ሀብት በጥናት በመለየት ኢኮኖሚያዊ ፋይዳቸውን ለማሳደግ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ማእድን ልማት ፅህፈት ቤት ገለፀ።

የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ታደሰ ካሳዬ ለኢዜአ እንደገለጹት ዞኑ ከአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት የማእድን ልየታ ጥናት እየሰራ ነው።

በዚህም ለኢንዱስትሪ ግብአትና ለግንባታ የሚያገለግሉ 17 ዓይነት ማእድናት እንደሚገኙ በጥናት መለየታቸውን ገልጸዋል።

በጥናት የተለዩት ማእድናትም ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚያገለግሉ ካዮሊን፣ ፑሚስ ፣ ሶዳ አሽ፣ ቢንቶናይት፣ ላይምስቶን የተሰኙ መሆናቸውን አብራርተዋል።

የማእድን ሀብቶቹን በማልማት ለስኳር፣ ለሲሚንቶ፣ ለሴራሚክስ ፋብሪካዎች እንዲውሉ ጥረት እየተደረገ መሆኑን አመልክተዋል።

እነዚህን ማዕድናትን አልምቶ ኢኮኖሚያዊ ጥቅማቸውን ለማሳደግ ባለፉት ዓመታት በማእድን ልማት ዘርፍ ለተሰማሩ 10 አነስተኛ እና መካከለኛ ደረጃ አልሚዎች ፈቃድ መሰጠቱን ጠቁመዋል።

የማእድን ልማቱን ውጤታማ ለማድረግ በዘርፉ ለተሰማሩ አልሚዎች የብድርና ሌሎችም ድጋፎች መመቻቸቱን አስታውቀዋል።

የማእድን ልማቱ ከአካባቢ ሥነ ምህዳር ጥበቃ ጋር በተናበበ መልኩ በማስኬድ በቁፋሮው የተጎዳ መሬትን መልሶ የማልማት ስራም ጎን ለጎን እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።

በአዳማ ሣይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የጂኦሎጂ ዲፓርትመንት ፔትሮሎጂስትና ጂኦ ኬሚስትሪ መምህርና ተመራማሪ (ዶ/ር) መለሰ አለማየሁ፣ የማዕድን ሀብት ለኢንዱስትሪ፣ ለግብርና፣ ለመሠረተ ልማት ግንባታ ግብአት በማዋል የውጭ ምንዛሬን ማሳደግ፣ ለተኪ ምርቶች ለማዋል ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን ጠቁመዋል።

ዩኒቨርሰቲው በተለይም በዞኑ የሚገኝ የማዕድን ሀብትን በጥናትና ምርምር በመለየት ለድህነት ቅነሳ እና ለሥራ ዕድል ፈጠራ እንዲውሉ ድርሻውን እየተወጣ ነው ብለዋል።

ከአዳማ ከተማ አስተዳደር ጋር በመተባበር ማዕድናትን በማጥናት የጂኦሎጂ፣ ጂኦኬሚስትሪ፣ ጂኦፊዚካል እና የጂኦቴክኒካል ካርታ ሥራ ማከናወንና መረጃ ማሰባሰብ መካሄዱን አመላክተዋል።

በጥናቱ ለኮንስትራክሽን፣ ለሲሚንቶ እና ለኮስሞቲክስ ኢንዱስትሪ ግብዓት የሚያገለግሉ ማእድናት ክምችት በስፋት እንዳለ መረጋገጡን አስታውቀዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.