🔇Unmute
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ እያደገ የመጣው የዲጂታል ግብይት ሥርዓት የንግድ እንቅስቃሴን ከማቀላጠፍ ባለፈ ከመጭበርበርና ከእንግልት እየታደጋቸው መሆኑን የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለጹ።
ነዋሪዎቹ መጪዎቹን የገና እና የጥምቀት በዓላት ግብይታቸውን በቴሌብር እና በሞባይል ባንኪንግ በመጠቀም ያለምንም እንግልት እያከናወኑ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል።
አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡት መካከል አቶ ገዛህኝ መካሻ እንደገለጹት፤ የዲጂታል ግብይት ሥርዓቱ በፈጠረው ምቹ ሁኔታ ማንኛውንም ክፍያ በቴሌብርና በሞባይል ባንኪንግ እንደሚፈጽሙ ገልጸዋል።

ይህም ጉልበትንና ጊዜን ከመቆጠብ ባለፈ፣ ተንቀሳቃሽ ገንዘብ በመያዝ ከሚገጥሙ ስጋቶችና ከአጭበርባሪዎች ራሳቸውን ለመከላከል እንዳስቻላቸው ጠቁመዋል።
በመሆኑም ለመጪዎቹ በዓላት የሚገዟቸውን ቁሳቁሶች በዲጂታል መንገድ እየፈጸሙ መሆኑን ተናግረዋል።
ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ዶክተር ሳሮን ሲሳይ በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል የነበሩ የክፍያ አገልግሎቶች በእንግልት የተሞሉና ጊዜን በአግባቡ ለመጠቀም የማይመቹ እንደነበሩ አስታውሰዋል።

አሁን ላይ ግን እያንዳንዱን አገልግሎት በዲጂታል መንገድ መፈጸም መቻሉ ሕይወትን በእጅጉ ቀለል እንዳደረገው ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ እያሳየች ያለውን ፈጣን ዕድገት ለማስቀጠል የዲጂታል ዓለምን መቀላቀሏ የሚያስደስት መሆኑን የገለጹት ደግሞ መምህርት ፍሬሕይወት ለማ ናቸው።

የዲጂታል ግብይት ሥርዓቱ ጥሬ ገንዘብ የመያዝ ልማዴን በማስቀረት ሁሉንም አገልግሎት በስልኬ እንዳገኝ አስችሎኛል ሲሉም አክለዋል።
የኢትዮ ቴሌኮም የሞባይል መኒ ቢዝነስ ዋና ኦፊሰር አቶ ብሩክ አድሃና፤ ተቋሙ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ የዲጂታል ሕልም እውን ለማድረግ በትጋት እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል።

እንደ ኦፊሰሩ ገለጻ፤ባለፉት አራት ዓመታት ከሀምሳ ሰባት ሚሊዮን በላይ በሆኑ የዲጂታል ክፍያ ደንበኞች አማካኝነት ከስድስት ትሪሊዮን ብር በላይ ግብይት ተከናውኗል።
መጪዎቹን የገናና የጥምቀት በዓላት ምክንያት በማድረግም ደንበኞች የዲጂታል ግብይቶችንም ሆነ ሌሎች አገልግሎቶችን ያለምንም መቆራረጥ እንዲያከናውኑ አስፈላጊው ዝግጅት መደረጉን አረጋግጠዋል።
Jul 17, 2025
Apr 24, 2025
አዲስ አበባ፤የካቲት 4/2017(ኢዜአ)፦ የሲሚንቶ ንግድ እና መሰረታዊ የፍጆታ እቃዎችን በተመለከተ የወጡ መመሪያዎች ገበያውን በማረጋጋትና የዋጋ ግሽበትን በመቀ...
Feb 12, 2025