የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ልዩ ዘገባ

የዲጂታል ግብይት ሥርዓት የንግድ እንቅስቃሴን አቀላጥፏል

Jan 9, 2026

IDOPRESS

🔇Unmute

አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ እያደገ የመጣው የዲጂታል ግብይት ሥርዓት የንግድ እንቅስቃሴን ከማቀላጠፍ ባለፈ ከመጭበርበርና ከእንግልት እየታደጋቸው መሆኑን የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለጹ።

ነዋሪዎቹ መጪዎቹን የገና እና የጥምቀት በዓላት ግብይታቸውን በቴሌብር እና በሞባይል ባንኪንግ በመጠቀም ያለምንም እንግልት እያከናወኑ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል።

አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡት መካከል አቶ ገዛህኝ መካሻ እንደገለጹት፤ የዲጂታል ግብይት ሥርዓቱ በፈጠረው ምቹ ሁኔታ ማንኛውንም ክፍያ በቴሌብርና በሞባይል ባንኪንግ እንደሚፈጽሙ ገልጸዋል።


ይህም ጉልበትንና ጊዜን ከመቆጠብ ባለፈ፣ ተንቀሳቃሽ ገንዘብ በመያዝ ከሚገጥሙ ስጋቶችና ከአጭበርባሪዎች ራሳቸውን ለመከላከል እንዳስቻላቸው ጠቁመዋል።

በመሆኑም ለመጪዎቹ በዓላት የሚገዟቸውን ቁሳቁሶች በዲጂታል መንገድ እየፈጸሙ መሆኑን ተናግረዋል።

ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ዶክተር ሳሮን ሲሳይ በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል የነበሩ የክፍያ አገልግሎቶች በእንግልት የተሞሉና ጊዜን በአግባቡ ለመጠቀም የማይመቹ እንደነበሩ አስታውሰዋል።


አሁን ላይ ግን እያንዳንዱን አገልግሎት በዲጂታል መንገድ መፈጸም መቻሉ ሕይወትን በእጅጉ ቀለል እንዳደረገው ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ እያሳየች ያለውን ፈጣን ዕድገት ለማስቀጠል የዲጂታል ዓለምን መቀላቀሏ የሚያስደስት መሆኑን የገለጹት ደግሞ መምህርት ፍሬሕይወት ለማ ናቸው።


የዲጂታል ግብይት ሥርዓቱ ጥሬ ገንዘብ የመያዝ ልማዴን በማስቀረት ሁሉንም አገልግሎት በስልኬ እንዳገኝ አስችሎኛል ሲሉም አክለዋል።

የኢትዮ ቴሌኮም የሞባይል መኒ ቢዝነስ ዋና ኦፊሰር አቶ ብሩክ አድሃና፤ ተቋሙ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ የዲጂታል ሕልም እውን ለማድረግ በትጋት እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል።


እንደ ኦፊሰሩ ገለጻ፤ባለፉት አራት ዓመታት ከሀምሳ ሰባት ሚሊዮን በላይ በሆኑ የዲጂታል ክፍያ ደንበኞች አማካኝነት ከስድስት ትሪሊዮን ብር በላይ ግብይት ተከናውኗል።

መጪዎቹን የገናና የጥምቀት በዓላት ምክንያት በማድረግም ደንበኞች የዲጂታል ግብይቶችንም ሆነ ሌሎች አገልግሎቶችን ያለምንም መቆራረጥ እንዲያከናውኑ አስፈላጊው ዝግጅት መደረጉን አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.