የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ልዩ ዘገባ

በክልሉ የተተገበሩ የግብርና ማሻሻያ ፕሮግራሞች ምርታማነትን አሳድገዋል

Jan 16, 2026

IDOPRESS

🔇Unmute

‎ዲላ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የተተገበሩ የግብርና ማሻሻያ ፕሮግራሞች የዘር ብዜትና የግብዓት አቅርቦትን በማሳለጥ ምርታማነትን እያሳደጉ መሆናቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ።

በብሔራዊ የምግብ ሥርዓት ማጠናከሪያ እና በተሳትፏዊ ግብርናና የአየር ንብረት ለውጥ ፕሮግራሞች የበጀት ድጋፍ የተገዙ ተሽከርካሪዎች በክልሉ ለሚገኙ 15 ወረዳዎች ተሰራጭተዋል።


ድጋፉም 10 መኪኖችና 12 ሞተር ሳይክሎችን ጨምሮ የተለያዩ ኮምፒውተሮችና የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችን ያካተተ ሲሆን የወረዳዎችን አቅም በማጎልበት የግብርና ምርታማነትን ለማጠናከር እንደሚያግዝ ተመላክቷል።

በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) ድጋፉን ባስረከቡበት ወቅት እንዳሉት፣ በፕሮግራሞቹ በዘር ብዜትና በግብዓት አቅርቦት ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል።

በክልሉ የምርጥ ዘር ፍላጎትን በራስ አቅም ለመሸፈን በሚደረገው ጥረት ስንዴና በቆሎን ጨምሮ አራት የሰብል አይነቶች ለአርሶ አደሩ ተደራሽ መደረጋቸውን አክለዋል።


የግብርናና ገጠር ትራንስፎርሜሽንን ለማረጋገጥም የግብርና ምርታማነት ማሳደግ ላይ በማተኮር የመስኖ አውታሮችን ለማስፋት መሰራቱን ጠቁመዋል።

ዛሬ ለወረዳዎቹ የተሰራጩት ተሽከርካሪዎችና የተለያዩ ግብአቶች በግብርና ልማት የተገኘውን ውጤት ለማጠናከር የጎላ ሚና እንዳላቸው አንስተዋል።

ወረዳዎችም ድጋፉን ለታለመለት ዓላማ ብቻ በማዋልና ገበያን መሰረት ያደረገ የግብርና ልማትን በማስፋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት እንዲያረጋግጡ አስገንዝበዋል።


በተሳትፏዊ ግብርናና የአየር ንብረት ለውጥ ፕሮግራም የተበረከተላቸው የሞተር ሳይክልና የኮምፒውተር ድጋፍ የልማት ሥራዎችን ለማቀላጠፍ እንደሚያስችል የገለጹት ደግሞ በጋሞ ዞን የካምባ ዙሪያ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሴሎ ይመር ናቸው።

ድጋፉ በዘር ብዜትና በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ የተገኘውን ተጨባጭ ውጤት ለማጠናከር ድርሻው የጎላ ነው ብለዋል።

በጌዴኦ ዞን የገደብ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ አብርሃም ደመቀ በበኩላቸው፤ በወረዳው የምግብ ሥርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም ድጋፍ የአርሶ አደሩን የመስኖ ልማት ተጠቃሚነት በማጠናከር ምርታማነቱን ለማሳደግ እያገዘ ነው ብለዋል።


ለአብነትም በፕሮግራሙ ተገንብቶ በተያዘው ዓመት ለአገልግሎት የበቃው የጨልጨሌ የመስኖ አውታር ከ60 በላይ አርሶ አደሮችን በማህበር በማደራጀት በአትክልት ልማት እንዲሰማሩ ማስቻሉን ጠቅሰዋል።

የተገነባው የመስኖ አውታርና ዛሬ የተደረገላቸው የመኪና ድጋፍ የግብርና ልማትን ለማጠናከር ድርሻው የጎላ መሆኑንም ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.