የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ልዩ ዘገባ

ዩኒቨርሲቲው የኢንዱስትሪ ምርታማነትን የሚያሳድጉ ብቁ ባለሙያዎችን እያፈራ ነው

Feb 13, 2026

IDOPRESS

🔇Unmute

አዲስ አበባ፤የካቲት 2/2018 (ኢዜአ)፡-የኢንዱስትሪውን ዘርፍ ምርታማነት የሚያሳድጉ ብቁ ባለሙያዎችን በማፍራት ረገድ ከፍተኛ ድርሻ እየተወጣ መሆኑን አዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ።

አስረኛው ዓለም አቀፍ የምርምር ኮንፈረንስ "ሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ እና ፈጠራ ለኢንዱስትሪ" በሚል መሪ ሀሳብ መካሄድ ጀምሯል።


የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ደረጃ እንግዳ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ ለሁለት ቀናት በሚቆየው በዚህ ኮንፈረንስ ላይ ከ96 በላይ የምርምር ሥራዎች ለውይይት የሚቀርቡ ሲሆን የልምድ ልውውጥ ለማድረግ ትልቅ ዕድል የሚፈጥር ነው፡።

ዩኒቨርሲቲው ትኩረቱን በምርምር እና በተግባር ተኮር ትምህርት ላይ ማድረጉን የጠቀሱት ፕሬዝዳንቱ፣ ይህም ተማሪዎች የኢንዱስትሪውን ችግር በቀጥታ መፍታት የሚችሉ የፈጠራ ሥራዎችን ይዘው እንዲወጡ እያገዘ መሆኑን ገልጸዋል።

ተማሪዎች ከንድፈ-ሀሳብ ባለፈ በዘመናዊ ላቦራቶሪዎች እንዲሰለጥኑ በመደረጉ፣ ለሥራ ዝግጁ የሆኑ ባለሙያዎች እየበቁ እንደሚገኙም አክለዋል።

በተጨማሪም በዩኒቨርሲቲው የሚወጡ የፈጠራ ውጤቶች ወደ ኢንዱስትሪው እንዲሸጋገሩ በማድረግ የምርት ሂደቱን ለማዘመን ጥረት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው ከተለያዩ ፋብሪካዎችና የቴክኖሎጂ ተቋማት ጋር በቅንጅት በመስራት የተማሪዎችን የተግባር ልምምድ ውጤታማ እያደረገ መሆኑንም አስረድተዋል።

በቀጣይም በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሆኑ የፈጠራ ሥራዎችን ለማፍለቅና የኢንዱስትሪ-ዩኒቨርሲቲ ትስስሩን ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።


የኢትዮጵያ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ሚልኬሳ ጃጋማ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በአዋጅ የተደገፈ የዩኒቨርሲቲ-ኢንዱስትሪ ትስስር በመፈጠሩ የኢንዱስትሪ ችግሮችን የሚያጠናና መፍትሄ የሚሰጥ የሰው ኃይል እየቀረበ መሆኑን ገልጸዋል።

በዚህ ረገድም የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ እያከናወነ ያለው ተግባር አመርቂ መሆኑን ጠቁመዋል።

የቤልጂየሙ ትራይዲል ሃውስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ማይክል ሎትስ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ በኢንዱስትሪው ዘርፍ ያስመዘገበቻቸው ለውጦች የሚታዩና የሚዳሰሱ መሆናቸውን ገልጸው ለዚህም ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 እና የአምስት ሚሊዮን ኮደሮች ኢኒሼቲቭ ትልቅ ማሳያዎች መሆናቸውን ጠቅሰዋል።


በአሁኑ ወቅት ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር በኢንዱስትሪ፣ በቤቶች ልማትና በሌሎች ዘርፎች በቅርበት እየሰሩ መሆኑን ጠቁመው፤ በቀጣይም ይህ ትብብር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.