የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ልዩ ዘገባ

በሲዳማ ክልል ከ34 ነጥብ 2 ሚሊዮን በላይ የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው የቡና ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል

Mar 11, 2026

IDOPRESS

🔇Unmute

ሀዋሳ፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል ከ34 ነጥብ 2 ሚሊዮን በላይ የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው የቡና ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን የክልሉ ቡና፣ ፍራፍሬና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን አስታወቀ፡፡

የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ መስፍን ቃሬ ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ከተለያዩ የግብርና ምርምር ማዕከላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው፡፡

ለመጪው ክረምት የሚተከሉ ከ34 ነጥብ 2 ሚሊዮን በላይ የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው የቡና ችግኞች መዘጋጀታቸውንም ተናግረዋል፡፡

ችግኞቹ የተዘጋጁት በክልሉ መንግስት፣ በማህበራት፣ በግል ባለሃብቶች እና 15ሺህ በሚጠጉ አርሶ አደሮች አማካይነት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በአርሶ አደሮች የሚዘጋጁት 23 ሚሊዮን የሚጠጉ የቡና ችግኞች መሆናቸውን ዳይሬክተሩ ጠቁመው፣ የተሻሻሉት የቡና ዝርያዎቹ በሽታን የሚቋቋሙና ምርታማነትን የሚያሳድጉ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

ከወንዶገነት፣ አዋዳና ጅማ ግብርና ምርምር ማዕከላት ጋር በመቀናጀት ምርታማነታቸው የተረጋገጡ የቡና ዝርያዎችን ከማላመድ ባለፈ የቴክኖሎጂ መንደሮችን በመፍጠር የቡና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡

በዚህም በሄክታር 8 ኩንታል ብቻ የነበረው የቡና ምርታማነት በአሁኑ ወቅት ወደ 10 ነጥብ 3 ኩንታል መድረሱን ገልጸው፣ በቀጣይ ሦስት ዓመታት ይህንን ወደ 15 ኩንታል ለማድረስ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡

ለችግኝ ተከላ ሥራ የሚሆኑ የጉድጓድ ቁፋሮ ሥራም መጠናቀቁን ያመለከቱት ዋና ዳይሬክተሩ፣ አሁን መጣል የጀመረው ዝናብ ቀጣይነት ካለው ከሚያዚያ 1 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የችግኝ ተከላ ሥራ ይጀመራል ብለዋል፡፡

በዚህም ያረጁ ቡናዎችን በመንቀል በአዲስ መልክ የመተካትና ከዚህ ቀደም ባህር ዛፍ በነበረባቸው ቦታዎችና በደጋማ አካባቢዎች ቡናን የማስፋፋት ሥራ በትኩረት እንደሚሰራ አስታውቀዋል፡፡


በሲዳማ ክልል የሸበዲኖ ወረዳ አርሶ አደር ዲልኬ ዲዳሞ ለተከላ የሚሆኑ ከ30ሺህ በላይ የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው የቡና ችግኞችንና የአፈር ማዳበሪያ ማዘጋጀታቸውን ተናግረዋል፡፡

ከ2001 ዓ.ም ጀምሮ በቡና ችግኝ ዝግጅት ሥራ እየተሳተፉ መሆናቸውን ገልጸው፣ በአቅራቢያቸው ከሚገኘው የመንግስት ችግኝ ጣቢያ የወሰዱት ተሞክሮ በልማት ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግረው ችግኞችን ለአካባቢው አርሶ አደሮች በማቅረብ የተሻለ ገቢ እጠብቃለሁ ብለዋል ፡፡

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.