የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ልዩ ዘገባ

ዓለም አቀፉ የሆርቲካልቸር ንግድ ትርዒት የኢትዮጵያን እምቅ አቅም ለዓለም ገበያ ለማስተዋወቅ ትልቅ ዕድል ይፈጥራል

Mar 25, 2026

IDOPRESS

🔇Unmute

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018(ኢዜአ)፦ 10ኛው ዓለም አቀፍ የሆርቲካልቸር የንግድ ትርዒት የኢትዮጵያን እምቅ አቅም ለዓለም ገበያ ይበልጥ ለማስተዋወቅና የንግድ ትስስርን ለማጠናከር ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥር የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፍያ ካሳ(ዶ/ር) ገለጹ።

የኢትዮጵያ አበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ አምራችና ላኪዎች ማህበር ከኤች.ፒ.ፒ. ዓለም አቀፍ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ይህ የንግድ ትርዒት ከዛሬ መጋቢት 15 እስከ 17 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ ተገልጿል።


በመክፈቻው የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፍያ ካሳ(ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ በአበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ ዘርፍ ያላትን እምቅ አቅም ይበልጥ ለማሳደግ መንግስት ለግሉ ዘርፍ ምቹ ምህዳር መፍጠሩን ገልጸዋል።

ለዚህም ዘርፉን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሚያደርገውን የግብርናና ገጠር ልማት ፖሊሲ እንዲሁም የአበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ ስትራቴጂ ተቀርጾ ወደ ሥራ መገባቱን ጠቁመዋል።

ኢትዮጵያ ወደ ውጭ ከምትልካቸው የሆርቲካልቸር ምርቶች ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እያገኘች መሆኑን ገልጸው፤ ይህ የንግድ ትርዒት አምራቾችን ከዓለም አቀፍ ገዢዎች ጋር በቀጥታ በማገናኘት እንደ ትልቅ ድልድይ ሆኖ ያገለግላል ብለዋል።

የኢትዮጵያ አበባ አትክልትና ፍራፍሬ አምራቾችና ላኪዎች ማህበር ዋና ዳይሬክተር ነጋ መኳንንት በበኩላቸው፤ ኤክስፖው ምርትና አገልግሎትን ከማስተዋወቅ ባለፈ በዘርፉ ያሉ ተዋናዮችን በአንድ ጣሪያ ስር በማገናኘት የንግድ ትስስርን ለማጠናከር ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።

ይህም ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ የተደገፈና ለዓለም ገበያ ተወዳዳሪ የሆነ የኢንዱስትሪ ግንባታ ለማካሄድ ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑንም አብራርተዋል።


የሆርቲካልቸር ዘርፍ ከቡና ቀጥሎ ለኢትዮጵያ ዋነኛው የውጭ ምንዛሪ ምንጭ ሲሆን፤ ባለፈው በጀት ዓመት 564 ነጥብ 89 ሚሊየን ዶላር ለሀገሪቱ ማስገኘቱ ጠቅሰዋል፡፡

ለሦስት ቀናት በሚቆየው በዚህ ንግድ ትርዒት ላይ ከ50 በላይ ሀገራት የተወከሉ ሲሆን፤ ከ150 በላይ የሀገር ውስጥና የውጭ አልሚ ባለሀብቶች፣ አምራቾች፣ የቴክኖሎጂ አቅራቢዎችና የፋይናንስ ተቋማት እንደሚሳተፉ ታውቋል።

በቆይታው ሰው ሰራሽ አስተውሎት(AI)፣ ዘላቂ ፋይናንስ፣ የምግብ ደህንነት፣ የባህር ጭነት ሎጂስቲክስ እና የአየር ንብረት ለውጥን በሚቋቋሙ የቴክኖሎጂ ፈጠራዎች ላይ ያተኮሩ ከፍተኛ ፋይዳ ያላቸው ውይይቶች እንደሚካሄዱ ይጠበቃል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.