የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ልዩ ዘገባ

የቻይና ባንክ በቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ፕሮጀክት ላይ ለመሳተፍ ፍላጎት አሳይቷል

Apr 1, 2026

IDOPRESS

🔇Unmute

አዲስ አበባ፤መጋቢት 23/2018 (ኢዜአ)፦የቻይና ባንክ (Bank of China) በቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ፕሮጀክት ላይ ለመሳተፍ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳለው አስታወቀ።

ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ እና ከገንዘብ ሚኒስቴር የተወጣጣ የኢትዮጵያ ልዑክ፣ ስለ አዲሱ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ግንባታ የገንዘብ ድጋፍ ዙሪያ ከቻይና ባንክ ጋር ውይይት አድርጓል።

በውይይቱ ወቅት የኢትዮጵያ ልዑክ ስለ ፕሮጀክቱ ቴክኒካዊ ንድፍ (design)፣ስለ ግንባታው የጊዜ ሰሌዳ እና ስለ አጠቃላይ የፋይናንስ መዋቅሩ ዝርዝር ማብራሪያ ሰጥቷል።

በተጨማሪም ፕሮጀክቱን ይበልጥ ውጤታማ፣በባንኮች ዘንድ ተቀባይነት ያለው (bankable) እና በረጅም ጊዜ የሀገሪቱን የፋይናንስ አቅም የማይጎዳ ለማድረግ የተከናወኑ የማሻሻያ ስራዎችን በተመለከተ ገለጻ ተደርጓል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ በበኩሉ ፕሮጀክቱ በቀጣናው ያለውን ከፍተኛ ፋይዳ በአጽንኦት ያነሳው ጉዳይ ነው።

አዲሱ አየር ማረፊያ ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ዘርፍ ያላትን መሪነት የሚያጠናክር ከመሆኑም በላይ ለንግድ፣ ለቱሪዝም እና ለአጠቃላይ የኢኮኖሚ እድገት ያለውን ሚና ልዑኩ አስረድቷል።

የቻይና ባንክ በፕሮጀክቱ ላይ ለመሳተፍ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳለው ገልጿል።

ባንኩ በአየር ማረፊያ ኢንቨስትመንቶች ላይ ልምድ እንዳለው ገልጾ፥ በአፍሪካ ከፍተኛ ተጽዕኖ ፈጣሪ በሆኑ መሰረተ ልማቶች ላይ ትኩረት እንደሚያደርግ አመልክቷል።

የአየር ማረፊያ ፕሮጀክት ከባንኩ ቅድሚያ ከሚሰጣቸው ጉዳዮች እና በትላልቅ የትራንስፖርት መሰረተ ልማት ፋይናንስ ካለው ልምድ ጋር በሚገባ እንደሚጣጣምም ነው ባንኩ ያስታወቀው።

በተጨማሪም ባንኩ የፕሮጀክቱ ዋና አስተባባሪ (Mandated Lead Arranger) ከሆነው ከአፍሪካ ልማት ባንክ ጋር የፋይናንስ ማዕቀፉን ለመረዳት እና በትብብር መስራት በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ዙሪያ እየተነጋገረ መሆኑን ጠቁሟል።

ውይይቱ በዋናነት የገንዘብ ድጋፍ በሚደረግበት ሁኔታ፣ ከሌሎች አበዳሪዎች ጋር በሚኖር ቅንጅት እና አስፈላጊ በሆኑና ጥንቃቄ በሚሹ መስፈርቶች ላይ በማተኮር ተካሄዷል።

ሁለቱም ወገኖች የቴክኒክ እና የፋይናንስ ውይይቶችን በተጠናከረ ሁኔታ ለማስቀጠል እና የቅርብ ግንኙነታቸውን ለማጠናከር ተስማምተዋል።

የቻይና ባንክ በገንዘብ ድጋፍ ጥቅሉ ውስጥ ለመሳተፍ ዝግጁ እንዲሆን ቀጣይነት ያለው የመረጃ ልውውጥ እና የጋራ ጥረት አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል።

በውይይቱ የቻይና ባንክ ለፕሮጀክቱ የፋይናንስ አቅርቦት ድጋፍ በማድረግ የበኩሉን እንደሚወጣ መግለጹን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.