
አዲስ አበባ ፤ጥር 3/2017 (ኢዜአ) ፦በኢትዮጵያ ጠንካራ የካፒታል ገበያ ስርዓት ለመገንባት የሌሎች አገራትን ተሞክሮ በራስ አውድ መተግበር እንደሚገባ የአፍሪካ የሰነደ ሙዓለ-ንዋይ ገበያ ማህበር ፕሬዝዳንት ሰልስቲያን ፔሪ ገለፁ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የኢትዮጵያ የሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያን ትናንት በይፋ አስጀምረዋል።
በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ በተደረገ የፓናል ውይይት ላይ የአፍሪካ የሰነደ ሙዓለ-ንዋይ ገበያ ማህበር ፕሬዝዳንት ሰልስቲያን ፔሪ እንዳሉት በኢትዮጵያ የህግ ማዕቀፍ ተዘጋጅቶ ስራው መጀመሩ በስኬት የሚነሳ ነው።
ይህም በአገሪቱ የሰነደ ሙዓለ ንዋይን ለመጀመር የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል።
በአለም የካፒታል ገበያ ሳይኖር ውጤታማ ኢኮኖሚ መገንባት አለመቻሉን አንስተው የተለያዩ ልምዶችን መቀመርና ከሌሎች አገራት መማር እንደሚቻል ተናግረዋል።
በአፍሪካ አብዛኛው አገራት አነስተኛ ገበያ ያላቸው መሆኑን አንስተው ሆኖም ትልቅ ገበያን ለመመስረት ጠንካራ የካፒታል ገበያ ከገነቡት ልምድን መውሰድ ይገባል ብለዋል።

በኢትዮጵያም ስኬታማ ከሆኑ አገራት ጥሩ ተሞክሮን በመቅሰም ለራስ በሚጠቅም አውድ መተግበር እንደሚገባም አስረድተዋል።
ከጠንካራ ህግና መመሪያዎች በተጨማሪ የካፒታል ገበያ ላይ እውቀት ያላቸው ባለሙያዎች እንዲበራከቱና የህብረተሰቡን የቁጠባ መጠን ማሳደግ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸው፤ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል።
በኢትዮጵያ የካፒታል ገበያውን የሚቆጣጠሩ አካላት በተቀናጀ አግባብ መስራት እንዳለባቸውም ገልፀዋል።
በአፍሪካ ከጥቂት አገራት በስተቀር የባንኮች ተቀማጭ ገንዘብ በቂ አለመሆኑን ጠቅሰው፤ ለዚህም የሰነደ ሙዓለ-ንዋይ ግብይት ወሳኝ መሆኑን አስረድተዋል።
የቁጠባ መጠንን ማሳደግና ፕራይቬታይዜሽንን ማጠናከር ለካፒታል ገበያ አስፈላጊ መሆኑንም ጠቁመዋል።
የአገር ውስጥ ኢንቨስተሮች ገበያውን በሚገባ ከደገፉ በአገር ውስጥ አቅም ኢኮኖሚውን ማጠናከር እንደሚቻልም ነው የተናገሩት።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ትልቅ ምጣኔ ሃብት ያላት አገር በመሆኗ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሆነ ኢኮኖሚ ለመገንባት የተጠናከረ የካፒታል ገበያ እንደሚያስፈልጋት አስረድተዋል።
ጅማ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለገበያ መቅረቡን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ቲጃኒ ተማም ተናገሩ...
Apr 24, 2026
ጅግጅጋ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኅብረት ሥራ ማኅበራትን በቴክኖሎጂና ሌሎች መስኮች የማጠናከር ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የሶማሌ ክልል ምክትል ርዕሠ መ...
Apr 22, 2026
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በስንዴ ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካዊያን በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን የአ...
Apr 15, 2026
አዶላ ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በበልግ አዝመራ ከ260 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ...
Apr 9, 2026