አመያ፤ የካቲት 29/2017 (ኢዜአ):-በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ኮንታ ዞን በተለያዩ የስራ ዘርፎች የተሰማሩ ሴቶች ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ገለፁ።
የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ሁሪያ አሊ በበኩላቸው ሴቶች በኢኮኖሚ እራሳቸውን እንዲችሉ እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል።
የዓለም አቀፍ የሴቶች ቀን “ፈጣንና ቀጣይነት ያለው ሁሉን አቀፍ ለውጥ በሴቶች ተሳትፎ ይረጋገጣል” በሚል መሪ ቃል በክልል ደረጃ በኮንታ ዞን በተለያዩ ኩነቶች እየተከበረ ነው።
በዓሉን አስመልክቶ በተዘጋጀው አውደ ርዕይና ባዛር ላይ ሴቶች የተለያዩ ምርታቸውን አቅርበዋል።
በአውደ ርዕዩ ላይ የተገኙት የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ሁሪያ አሊ እንደገለፁት፤ ሴቶች በኢኮኖሚ ራሳቸውን እንዲችሉ የድጋፍና ክትትል ስራዎች በትኩረት እየተሰሩ ነው።
በተለያዩ ዘርፎች የመሰማራት ዕድሎች እየተመቻቹ እንዳሉና የተሰማሩትም ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸው ይህ ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን አስረድተዋል ።
በዚህም በዞኑ በተለያዩ ዘርፎች የተሰማሩ ሴቶች ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ሚኒስትር ዴኤታዋ ገልፀዋል።
የኮንታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታከለ ተስፉ በዓሉ በሴቶች እየተሰሩ ያሉ ስራዎችን ለመመልከት፣ የገበያ ትስስር ለመፍጠርና ያሉባቸውን ችግሮች ለይቶ ለመፍታት ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል።
በዞኑ የሴቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በከተማና በገጠር ሰፊ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ጠቁመው፣ የመሸጫ ቦታና ሌሎች ችግሮችን ለመፍታት ይሰራልም ብለዋል።
በዞኑ በኤል ሀንቻኖ ወረዳ በሾታ ሻሾ ቀበሌ የሴቶች ልማት ህብረት ሰብሳቢ ወይዘሮ ጎቶሬ ጎደቶ ከ300 በላይ የሆኑ ሴቶች በመደራጀት በሰብልና በእንስሳት እርባታ ስራ ላይ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በአጠቃላይ ባላቸው ስድስት ሄክታር መሬት ላይም የበጋ መስኖ ስንዴን ጨምሮ በበግ ማሞከት፣ በአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም ቡናን ጨምሮ እያለሙ መሆናቸውን ገልጸዋል።
አሁን ላይ የቤተሰብን ወጪ ሸፍነው ቀሪውን ገንዘብ እየቆጠቡ ልጆቻቸውን ለማስተማር ዕድል ማግኘታቸውን ተናግረዋል።
በተሰጣቸው የስልጠና ድጋፍ ታግዘው የፈሳሽ ሳሙና ማምረት በመጀመራቸው ተጠቃሚ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ ወይዘሮ ትዕግስት ዶኖቾ ናቸው።
ከስድስት ወር በፊት በ60 ሺህ ብር የጀመሩት ስራ አሁን ላይ ካፒታላቸውን ከሶስት እጥፍ በላይ በማሳደግ ለሰባት ሰዎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል መፍጠራቸውን ተናግረዋል።
ወይዘሮ ዘይቱ ብሩ በበኩላቸው ባህላዊ ልብስ በመስራት እንደሚተዳደሩ ገልፀው ለአስር ሰዎች የስራ እድል መፍጠራቸውንና "ሴቶች ሁኔታዎችን ተቋቁመውና ወስነው ከሰሩ ውጤታማ መሆን ይችላሉ" ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
አዲስ አበባ፤ የካቲት 20/2017(ኢዜአ)፦ የቁልፍ መሰረተ ልማቶች ጥበቃ አዋጅን ሥራ ላይ ለማዋል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስ...
Feb 28, 2025
ደሴ፤ የካቲት 16/2017 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ወሎ ዞን በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት የተሻለ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዓሊ መኮንን ገለ...
Feb 24, 2025
አሶሳ ፤ የካቲት 15/2017(ኢዜአ):- የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ችግር ፈቺ ስራዎችን እንዲያከናውኑ እየተሰራ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 4/2017(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ቀንድ የልማት ትስስርና የኢኮኖሚ ውህደት የመሪነት ሚናዋን እየተወጣች እንደምትገኝ የአፍሪካ ቀንድ...
Feb 12, 2025