
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 4/2017 (ኢዜአ) ፦በኢንዱስትሪ ዘርፉ የተገኙ ውጤታማ ስራዎችን ለማጠናከር እየተሰራ መሆኑን የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ እና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ ጃንጥራር አባይ ገለጹ፡፡
በአዲስ ዓለምአቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ከመጋቢት 29 ጀምሮ "ከሸማችነት ወደ አምራችነት" በሚል መሪ ሐሳብ ሲካሄድ የቆየው የኢትዮጵያ - አዲስ አበባ ታምርት የ2017 ዓ.ም የአምራች ኢንዱስትሪዎች አውደ-ርዕይ ተጠናቋል፡፡
በማጠቃለያ መርሐ ግብሩ ላይ ከጥቃቅንና አነስተኛ ወደ አነስተኛ፣ ከአነስተኛ ወደ መካከለኛ እና ከመካከለኛ ወደ ከፍተኛ የደረጃ ሽግግር ላደረጉ አምራቾች እና በከተማዋ ከፍተኛ አፈጻጸም ላስመዘገቡ ትላልቅ ኢንዱስትሪዎች እውቅና ተሰጥቷል፡፡
የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ እና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ ጃንጥራር አባይ በዚሁ ወቅት፤ አምራች ኢንዱስትሪዎች ለዘላቂ የሥራ ዕድል ፈጠራና ለቴክኖሎጂ ሽግግር ጉልህ ሚና በማበርከት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ ከ3 ሺህ 700 በላይ ኢንዱስሪዎች መኖራቸውን ያነሱት ምክትል ከንቲባው የማምረት አቅማቸው ከ64 በመቶ ላይ መድረሱን ጠቅሰዋል።
ኢንዱስትሪዎቹ ተኪ ምርትና ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን በማምረት ለሀገር ኢኮኖሚ ዕድገት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኙ ገልጸዋል።
የኢንዱስትሪዎቹን የማምረት አቅም ለማሳደግና ለዘርፉ መነቃቃት የሚያግዝ የኢንዱስትሪ ፖሊሲ ተቀርጾ ወደ ስራ መገባቱን አንስተዋል።
በአውደርዕዩ የገበያ ትስስርና ምርትን የማስተዋወቅ ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቁመው መጪውን የፋሲካ በዓል ምክንያት በማድረግ በመዲናዋ በተለያዩ አካባቢዎች ባዛርና አውደርዕይ እንደሚካሄድ ተናግረዋል፡፡
አምራች ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅማቸውን ይበልጥ ለማላቅ መሥራት እንዳለባቸው የገለጹት ምክትል ከንቲባው፥ የከተማ አስተዳደሩ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቁመዋል፡፡
በመዲናዋ በኢንዱስትሪ ዘርፉ የተገኙ ውጤታማ ስራዎችን ዘላቂ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡
በመድረኩ በወጪ ንግድ፣ተኪ ምርቶችን በማምረት፣ በስራ ዕድል ፈጠራ፣በቴክኖሎጂ ሽግግር እና በሌሎች መስፈርቶች ለተሻሉ አምራች ኢንዱስትሪዎች እውቅና ተሰጥቷል፡፡
የዘናጭ ማኑፋክቸሪንግ ባለቤትና ስራ አስኪያጅ ተስፋዬ አባቴነህ፥ በሰሩት ስራ እውቅና ማግኘታቸውን ጠቁመው ድርጅቱ ተኪ ምርቶችን ከማምረት አኳያ አመርቂ ስራዎችን በመስራት ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡
የተሰጣቸው እውቅና ድርብ ኃላፊነት መሆኑን ጠቁመው በቀጣይ ድርጅታቸውን በማስፋፋት ተጨማሪ ስራ ዕድሎችን ለመፍጠር መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል፡፡
የብራስ ጋርመንት ተወካይ ሳምራዊት ንጉስ በበኩሏ፥ ድርጅታቸው በጨርቃጨርቅ ዘርፍ ከ300 በላይ ለሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ጠቁመዋል፡፡
ከመካከለኛ ወደ ከፍተኛ አምራችነት የተሸጋገሩት የሉሲያን ኮንስትራክሽን የግል ማህበር ስራ አስኪያጅ መሠረት አበበ፤ የደረጃ ሽግግሩ ከበርካታ ውጣውርዶች በኋላ የተገኘ መሆኑን ጠቅሰው ለላቀ ስኬት እንደሚሰሩ ተናግረዋል፡፡
ወደ መካከለኛ አምራችነት የተሸጋገሩት የኃይለሥላሴ እና ጓደኞቹ የድንጋይ ቅርጻቅርጽ ስራ ሕብረት ማህበር ስራ አስኪያጅ ኃይለ ሥላሴ ጣሰው፥ እውቅናው የተሻለ ምርት ለማምረትና ተጨማሪ የሥራ ዕድል ለመፍጠር እንደሚረዳቸው ገልጸዋል፡፡
የማርታ ሳምሶንና ጓደኞቻቸው የድንጋይ ቅርጻቅርጽ ሽርክና ማህበር ስራ አስኪያጅ ማርታ ታለጌታ በበኩላቸው ድርጅታቸው፥ ወደ መካከለኛ አምራችነት ማደጉን ጠቅሰው፥ ለምርት ጥራትና ተወዳዳሪነት እንደሚተጉ ጠቁመዋል፡፡
ጅማ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለገበያ መቅረቡን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ቲጃኒ ተማም ተናገሩ...
Apr 24, 2026
ጅግጅጋ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኅብረት ሥራ ማኅበራትን በቴክኖሎጂና ሌሎች መስኮች የማጠናከር ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የሶማሌ ክልል ምክትል ርዕሠ መ...
Apr 22, 2026
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በስንዴ ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካዊያን በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን የአ...
Apr 15, 2026
አዶላ ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በበልግ አዝመራ ከ260 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ...
Apr 9, 2026