
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2017(ኢዜአ)፦ መንግስት የትራንስፖርት፣ የግብርና ንግድ ፋይናንስ፣ የኢነርጂ ዘርፎችን ጨምሮ የግሉ ዘርፍ ኢንቨስትመንትን ለማሳደግ ቁርጠኛ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ገለጹ።
በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ካለው የዓለም ባንክ ግሩፕ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብሰባ ጎን ለጎን በአቶ አህመድ ሽዴ የተመራው ከፍተኛ የልዑካን ቡድን ከዓለም አቀፉ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን ዋና ዳይሬክተር ማክታር ዲዮፕ ጋር ተወያይቷል።
በውይይቱም ኢትዮጵያ እየተገበረችው ስላለው የኢኮኖሚ ሪፎርም እና የግሉን ዘርፍ ኢንቨስትመንት ለማነቃቃት እየተከናወኑ ስላሉ ማሻሻያዎች መክረዋል።

አቶ አህመድ ሽዴ ኢኮኖሚውን ለማዘመን እየተተገበረ ስላለው ሀገር በቀል ማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ገለጻ ያደረጉ ሲሆን ገበያ መር ኢኮኖሚ ከማስፈን አንጻር የተመዘገበውን የላቀ አፈጻጸምም አንስተዋል።
በተለይም በግሉ ዘርፍ በተሰማሩ ኢንቨስተሮች የታየው አዎንታዊ ፍላጎት የወጪ ንግድ እንዲጨምር ምክንያት እንደሆነም ገልጸዋል።
መንግስት የትራንስፖርት፣ የግብርና ንግድ ፋይናንስ፣ የኢነርጂ ዘርፎችን ጨምሮ የግሉ ዘርፍ ኢንቨስትመንትን ለማሳደግ ቁርጠኛ መሆኑንም አብራርተዋል።
በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ለግሉ ዘርፍ የተዘረጋውን ምቹ የማክሮ ኢኮኖሚ ሁኔታ ከግምት በማስገባት በኢትዮጵያ ጠቃሚ እና ወሳኝ ኢንቨስትመንቶችን ለመደገፍ ኮርፖሬሽኑ የሚያደርገውን ጥረት በበለጠ በሚያጠናከርበት ሁኔታ ላይም መክረዋል።

ዋና ዳይሬክተሩ በበኩላቸው ኢትዮጵያ ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር የምታደርገውን ጥረት አድንቀው የኢንቨስትመንት ምህዳሩን የበለጠ ለማሻሻል እና የግሉ ዘርፍ የሚመራውን ሁለንተናዊ ልማት ለማጠናከር ቀጣይነት ያለው ጥረት አስፈላጊ መሆኑን አመልክተዋል።
ኮርፖሬሽኑ አስፈላጊውን የቴክኒክ ድጋፍ አጠናክሮ ለመቀጠል እና ያሉትን አማራጮች በመጠቀም በኢትዮጵያ ለሚደረገው የኢንቨስትመንት ጥረቶች ድጋፍ ለማድረግ ያለውን ቁርጠኝነትም ገልፀዋል።
አክለውም ፍላጎት ካሳዩ የሁለትዮሽ እና የባለብዙ ወገን የልማት አጋሮች ጋር በዕቅድ በተያዘው አዲሱ የዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክት ዙሪያ ኮርፖሬሽኑ የጋራ ፋይናንስ ዕድሎችን ለመጠቀም ዝግጁ መሆኑንም ተናግረዋል።
ሁለቱም ወገኖች በከፍተኛ እና ቴክኒካል ደረጃ ተቀራርቦ በመስራት በኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች እና በወሳኝ የኢንቨስትመንት እድሎች ዙሪያ ትብብራቸውን ለማጠናከር መስማማታቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
የፋይናንስ ተቋማቱ ዓመታዊ ስብሰባ የተለያዩ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ዛሬ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል።
አዲስ አበባ፤ሰኔ 2 /2018 (ኢዜአ)፦የዕቃ ማከማቻ ደረሰኝ ሥርዓት ደንብ የግብርና ኢኮኖሚ ሽግግርን በማሳለጥና የገጠር ልማትን በማጎልበት አርሶ አደሮችን ተጠ...
Jun 10, 2026
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በመዲናዋ የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥን በማላቅ የተገልጋዮችን እርካታ የሚያሳድጉ ሰው ተኮር ተግባራት ተጠናክረው እንደ...
Jun 9, 2026
ሀዋሳ ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ) ፦በይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ኢንዱስትሪ ማቀነባበሪያ ፓርክ ከአምራች ኢንዲስትሪዎች ጋር በተፈጠረላቸው የገበያ ትስስር ...
Jun 6, 2026
ነገሌ ቦረና፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ አገልግሎት መጀመር የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ የበለጠ የሚያ...
May 28, 2026