
ወላይታ ሶዶ፤ግንቦት 4/2017(ኢዜአ)፦የወላይታ ሶዶ ግብርና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ኮሌጅ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በመሳተፍ የአካባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚ ከማድረግ ባለፈ የውስጥ ገቢውን እያሳደገ መሆኑን አስታወቀ።
የኮሌጁ ዲን አሉላ ታፈሰ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፥ ኮሌጁ ከመማር ማስተማር ሥራ በተጨማሪ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በእንስሳትና በዶሮ ልማት ውጤታማ ሥራ እያከናወነ ይገኛል።
በመርሃ ግብሩ የሚያመርታቸውን ምርቶች ለማህበረሰቡ ከማቅረብ ባለፈ በዘርፉ ላይ የህብረተሰቡን ግንዛቤ የማሳደግ ተግባር እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።
የሥጋ ዶሮዎችን፣ እንቁላልና የወተት ምርቶችን ጨምሮ የተለያዩ አትክልቶችን በማምረት ለአካባቢው ነዋሪዎች በቅናሽ ዋጋ በማቅረብ ገበያ የማረጋጋት ሥራ እያከናወነ መሆኑንም አመልክተዋል።
ኮሌጁ የወተት ምርት ለህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እንደሚያቀርብ ገልጸው፣ በዚህም ለአካባቢው ማህበረሰብ የሚሰጠውን አገልግሎት ከማጠናከር ባለፈ የኮሌጁን የውስጥ ገቢ እያሳደገ ነው ብለዋል።
ኮሌጁ በሚያከናውናቸው የሌማት ትሩፋት ሥራዎች ከ100 በላይ ለሚሆኑ የአካባቢው ነዋሪዎች ቋሚ እና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፍጠሩንም አሉላ (ዶ/ር) ተናግረዋል።
በእንስሳት እርባታ ዘርፍ ሰፋፊ ሥራዎች መጀመራቸውን የገለጹት ደግሞ በኮሌጁ የእንስሳት እርባታ ባለሙያ አቶ በረከት በቀለ፥ ህብረተሰቡ በኮሌጁ የሌማት ትሩፋት ሥራ በተለያየ መንገድ ተጠቃሚ እየሆነ ነው።
ኮሌጁ ምርቶችን በዝቅተኛ ዋጋ ከማቅረብ ባለፈ በዘመናዊ የእንስሳት እርባታ ላይ የህብረተሰቡን ግንዛቤ በማሳደግ ለሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ስኬታማነት የበኩሉን እየተወጣ መሆኑንም አመልክተዋል።
ኮሌጁ ወተትና እንቁላልን ጨምሮ የተለያዩ የግብርና ምርቶችን በቅናሽ ዋጋ በማቅረብ ገበያውን እያረጋጋ መሆኑን የገለጹት ደግሞ ወይዘሮ ማለዳወርቅ ሉቃስ የተባሉ የአካባቢው ነዋሪ ናቸው።
ህብረተሰቡ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በዘላቂነት ተጠቃሚ እንዲሆን ግንዛቤውን ከማሳደግ ባለፈ የዘር ድጋፍ እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።
ወይዘሮ ሻሼ ሻጎ የተባሉ ነዋሪ በበኩላቸው፥ ኮሌጁ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር እያከናወነ ባለው ተግባር የሥራ ዕድል ማግኘታቸውን ገልጸዋል።
ከዚህ ቀደም በጥቃቅን የችርቻሮ ንግድ ሥራ ተሰማርቼ በማገኛት ጥቂት ገንዘብ ቤተሰብ ለማስተዳደር እቸገር ነበር ያሉት ወይዘሮ ሻሼ፣ አሁን ላይ በተፈጠረላቸው የሥራ ዕድል በሚያገኙት ገቢ ያለስጋት ኑሯቸውን እየመሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።
የወላይታ ሶዶ ግብርና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ኮሌጅ የተሻሻሉ የግብርና አሰራርና ቴክኖሎጂዎችን ለማህበረሰቡ ተደራሽ ከማድረግ ባለፈ ሥራውን ለማስፋፋት ግብ ጥሎ እየሰራ መሆኑም ታውቋል።
ጅማ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለገበያ መቅረቡን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ቲጃኒ ተማም ተናገሩ...
Apr 24, 2026
ጅግጅጋ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኅብረት ሥራ ማኅበራትን በቴክኖሎጂና ሌሎች መስኮች የማጠናከር ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የሶማሌ ክልል ምክትል ርዕሠ መ...
Apr 22, 2026
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በስንዴ ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካዊያን በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን የአ...
Apr 15, 2026
አዶላ ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በበልግ አዝመራ ከ260 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ...
Apr 9, 2026