
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ሀገር በቀል ሰው ሰራሽ አስተውሎትን በማልማት ከአህጉራዊው አጀንዳ 2063 ግቦች ጋር የተጣጣመ ውጤት እያስመዘገበች መሆኑን የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር ሰልማ ማሊካ ሃዳዲ ገለጹ፡፡
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር እና የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በጋራ ያዘጋጁት በምስራቅ አፍሪካ ትልቁ ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ኤክስፖ 2025 በአዲስ አበባ ተከፍቷል፡፡
በኤክስፖው ሁለተኛ ቀን ውሎ “አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን ለአፍሪካ ብልጽግና እና ትብብር” በሚል ጭብጥ የአፍሪካን የሰው ሰራሽ አስተውሎት እንቅስቃሴ የተመለከተ መርሃ ግብር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት ተካሂዷል።
የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር ሰልማ ማሊካ ሃዳዲ በመርሃ ግብሩ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ኢትዮጵያ ያዘጋጀችው ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ኤክፖ ጠቃሚና ወቅቱን የዋጀ ነው ብለዋል፡፡

በአፍሪካ አካታችና ዘላቂ የሰው ሰራሽ አስተውሎት በመገንባት ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት ኢትዮጵያ የመሪነት ሚናዋን እየተወጣች መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ሰው ሰራሽ አስተውሎት በጂኦ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች አንዱ የለውጥ ኃይል እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት የሀገራት የብሔራዊ ጥቅም ማስከበሪያ፣ ኢኮኖሚ ሉዓላዊነት ማረጋገጫ፣ የደህንነት ዋስትና የትኩረት ማዕከል ሆኗልም ብለዋል፡፡
በአፍሪካ ኢኮኖሚያዊ ሽግግርን በማቀላጠፍ በሁሉም ዘርፍ ተጨባጭ ውጤት ለማስመዝገብ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎችን በትብብር ገቢራዊ ማድረግ ይገባል ነው ያሉት፡፡
በአፍሪካ ከፍተኛ የሥራ እድል በመፍጠር የሕብረቱን አጀንዳ 2063 እውን ለማድረግ ለሰው ሰራሽ አስተውሎት እድገት ምቹ ሁኔታ መፍጠር እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡

የአፍሪካ ሕብረት እ.አ.አ በ2024 አህጉራዊ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ስትራቴጂ ማጽደቁን ተናግረዋል፡፡
በአፍሪካ አካታችና ዘላቂ እድገት ለማረጋገጥ ምቹ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ሥነ ምህዳር መፍጠር እንደሚገባ ገልጸው፤ አፍሪካ በታዳሽ ኃይል፣ በወጣት የሰው ኃይል እና በማዕድን እምቅ አቅም እንዳላት አውስተዋል።
በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ስትራቴጂና አጀንዳ 2063ን ማሳካት የሚያስችል የሰው ሰራሽ አስተውሎት ልማት ላይ መሆኗን ተናግረዋል፡፡
ሀገር በቀል የሰው ሰራሽ አስተውሎት ልማት ለአፍሪካ እድገት ወሳኝ መሆኑን አንስተው፤ ኢትዮጵያ በዘርፉ የብዝሃ ባህል፣ ቋንቋና የብዝሃ ዘርፍ ልማትን በማካተት በአስደናቂ መንገድ ላይ መሆኗን ገልጸዋል፡፡
ይህም ኢትዮጵያ ሀገር በቀል ሰው ሰራሽ አስተውሎትን በማልማት ከአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063 ግብ ጋር የተጣጣመ ውጤት እያስመዘገበች መሆኗን ያሳያል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ሰው ሰራሽ አስተውሎት ቅንጦት ሳይሆን የመጪው ዘመን መወዳደሪያ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ቴክኖሎጂው በፈጠራ፣ በትምህርት፣ ጤና፣ ግብርና፣ ፋይናንስ፣ በደህንነትና ብሔራዊ ጥቅምን በማስከበር የጎላ አበርክቶ እንዳለውም አንስተዋል፡፡
ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አነሳሽነት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩትን በማቋቋም ሰው ሰራሽ አስተውሎት በልማት ላይ ጉልህ ሚና እንዲጫወት አድርጋለች ብለዋል፡፡
በአህጉሪቱ አካታችና ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ ሰው ሰራሽ አስተውሎት ወሳኝ መሆኑን ገልጸው፤ ኢትዮጵያ በ2030 የአፍሪካ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የልህቀት ማዕከል የመሆን ራዕይ መሰነቋን ተናግረዋል፡፡
ኢትዮጵያ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎችን በመቅረጽ በዘርፉ ላይ እመርታዊ ለውጥ ማስመዝገቧን ጠቅሰው፤ ለሌሎች ሀገሮች ልምዷን ለማካፈል ዝግጁ መሆኗንም አረጋግጠዋል፡፡
ጅማ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለገበያ መቅረቡን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ቲጃኒ ተማም ተናገሩ...
Apr 24, 2026
ጅግጅጋ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኅብረት ሥራ ማኅበራትን በቴክኖሎጂና ሌሎች መስኮች የማጠናከር ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የሶማሌ ክልል ምክትል ርዕሠ መ...
Apr 22, 2026
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በስንዴ ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካዊያን በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን የአ...
Apr 15, 2026
አዶላ ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በበልግ አዝመራ ከ260 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ...
Apr 9, 2026