
ጋምቤላ፤ግንቦት 21/2017(ኢዜአ)፡-በጋምቤላ ክልል ያለው ሰፊ የዓሳ ሀብት በቴክኖሎጂ ታግዞ በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዲውል የተጀመረው ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ገለጸ።
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ (ዶ/ር) በጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጽህፈት ቤት የተገነባውን ዘመናዊ ዲጂታል ስማርት የኮሙኒኬሽን ማሳለጫ ክፍል ስራ በማስጀመር በክልሉ ዓሳ ሀብት ልማት ዙሪያ ከክልሉ አመራሮች ጋር ተወያይተዋል።
በዚህ ወቅት ሚኒስትር ዴኤታው፥በክልሉ ያለው እምቅ የዓሳ ሀብት በቴክኖሎጂ ታግዞ የሚፈለገውን ጥቅም እንዲያስገኝ እየተደረገ ያለው ጥረት አበረታች መሆኑን ተናግረዋል።
ለዚህ መሳካት የሚኒስቴሩ ድጋፍ ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል ብለዋል።
ሚኒስቴሩ ቀደም ሲል በክልሉ የዓሳ ሀብት ልማቱን ለማዘመን የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ ሶስት የዓሳ ማቀነባበሪያና የግብይት ማዕከላት ግንባታን ጨምሮ የዓሳ ማጥመጃና ማቆያ የቴክኖሎጂ ግብዓቶችን ድጋፍ ማድረጉን አስታውሰዋል።
በቀጣይም የዘርፉን ልማት በማዘመን ሀብቱ ለክልሉ ብሎም ለሀገር የኢኮኖሚ ግንባታ እንዲውል እየተደረገ ላለው ጥረት ሚኒስቴሩ የጀመራቸውን ሁለንተናዊ ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።
የቴክኖሎጂ ግብዓቶችን ከመደገፍ ባለፈም በዘርፉ ለተሰማሩ ወጣቶች የገበያ ትስስር እንዲፈጠርላቸው ጭምር እገዛ እንደሚደረግም ሚኒስትር ዴኤታው ገልጸዋል።
የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር) በበኩላቸው፥ በክልሉ ሰፊ የዓሳ ሀብት ቢኖርም በዘመናዊ መልኩ በማልማትና ጥቅም ላይ በማዋል ረገድ ውስንነቶች መኖራቸውን አንስተዋል።
የዓሳ ሀብቱን ዘመናዊ የገበያ ሰንሰለት በመጠቀም ወደ ገበያ የማቅረቡ ስራ እንዳለ ሆኖ በቋንጣ መልክ እየተዘጋጀ ለገበያ እየቀረበ እንደሚገኝም ገልጸዋል።
በመሆኑም በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የተጀመሩት የቴክኖሎጂ ድጋፍና እገዛዎች እንዲጠናከሩ ምክትል ርዕሰ መስተዳደሩ ጠይቀዋል።
በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እየተደረጉ ካሉት የቴክኖሎጂ ግብዓት ድጋፎች በተጨማሪ የቴክኒክ እገዛ ጭምር ያስፈልጋል ያሉት ደግሞ የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ኮሚሽን ኮሚሽነር ፖል ጋሪ ናቸው።
በጋምቤላ ክልል በዓመት እስከ 20 ሺህ ቶን ዓሳ ማምረት የሚያስችል አቅም እንዳለ ከክልሉ እንስሳትና ዓሳ ሀብት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
ጅማ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለገበያ መቅረቡን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ቲጃኒ ተማም ተናገሩ...
Apr 24, 2026
ጅግጅጋ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኅብረት ሥራ ማኅበራትን በቴክኖሎጂና ሌሎች መስኮች የማጠናከር ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የሶማሌ ክልል ምክትል ርዕሠ መ...
Apr 22, 2026
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በስንዴ ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካዊያን በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን የአ...
Apr 15, 2026
አዶላ ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በበልግ አዝመራ ከ260 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ...
Apr 9, 2026