አርባ ምንጭ፤ ግንቦት 27/2017(ኢዜአ)፦ አመራሩ በለውጥ እሳቤ ታግዞ ለውጥ ፈጣሪ ማህበረሰብ የመፍጠር ሃላፊነቱን በአግባቡ መወጣት እንዳለበት የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል አስታወቁ።
በአርባ ምንጭ ከተማ ለሦስት ቀናት ሲሰጥ የቆየው የፐብሊክ ኢንተርፕሪነርሽፕና ኢኖቬሽን ስነ-ምህዳር ግንባታ የአመራሮች ስልጠና ተጠናቋል።
በማጠቃለያ መድረኩ የተገኙት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ባስተላለፉት መልዕክት አመራሩ በለውጥ እሳቤ ታግዞ ለውጥ ፈጣሪ ማህበረሰብ የመፍጠር ሃላፊነቱን በአግባቡ ሊወጣ ይገባል ብለዋል።
የበለጸገ ክልልና ሀገር እንዲፈጠር በየደረጃው ያለው አመራር ጊዜውን የዋጀ የዕውቀትና ክህሎት ትጥቅ በመታጠቅ ለህብረተሰቡ ፈጠራ የታከለበት የሥራ ምህዳር መፍጠር ይኖርበታል ሲሉም አክለዋል።
በማያቋርጥ የለውጥ ሂደት ውስጥ ነን ያሉት ሚኒስትሯ፣ አመራሩ በየአካባቢው ያሉ ፀጋዎች ለህዝብ ጥቅም እንዲውሉ በማድረግ ታሪካዊ ሃላፊነቱን መወጣት እንዳለበትም አስገንዝበዋል።
የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ከመንግስት ሀብት የሚፈልጉ ሳይሆን የራሳቸውን ሀብት የሚፈጥሩ መሆን እንዳለባቸው ጠቁመው፣ በየአካባቢው ያሉ ፀጋዎችን ጥቅም ላይ ለማዋል በሚሰራው ሥራ በቴክኖሎጂ ሽግግር የበኩላቸውን መወጣት እንዳለባቸው ገልጸዋል።
በለውጥ እሳቤ መሰረት የሥራ ዕድልን ከፈጠራ ጋር በማስተሳሰር ውጤታማ ሥራዎችን ለማከናወን ከአመራሩ ብዙ ይጠበቃል ሲሉም ተናግረዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ በበኩላቸው የአመራር ስልጠና በሀገር ደረጃ የተጀመረውን የለውጥ እሳቤ በአግባቡ በመረዳት ለችግሮች ሀገር በቀል መፍትሄ መስጠት እንደሚያስችል ገልጸዋል።
ባለፉት ሰባት ዓመታት በሀገር ደረጃ የነበሩ ስብራቶችን ለመጠገን ሥራዎች ሲሰሩ መቆየታቸውን ገልጸው፣ በዚህም ፈተናን ወደ ዕድል ዕዳን ወደ ምንዳ መቀየር ተችሏል ብለዋል።
በክልሉ ልማትን በማጠናከር ህዝብን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ጸጋዎች እንዳሉ ጠቁመው፣ አመራሩ በስልጠና ባገኘው እውቀት ታግዞ ጸጋዎችን በማልማት ለሥራ አጥነት ችግር መፍትሄ መስጠት እንዳለበት አሳስበዋል።
ስልጠናውን ያልወሰዱ ቀሪ አመራሮችን በማሰልጠን የለውጡ እሳቤ ወጥነት ባለው መንገድ እንዲሳካ የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባም ጠቁመዋል።
የሥራ አጥነት ችግርን በቅጥር ብቻ ማስወገድ አይቻለም ያሉት የፌደራል ኢንተርፕሪነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ሀሰን ሁሴን(ዶ/ር) ለዜጎች ምቹ የፈጠራ ምህዳር መፍጠር ያስፈልጋል ነው ያሉት።
ለወቅቱ ችግሮች ወቅቱን የሚመጥን መፍትሄ በመስጠት አመራሩ ስልጠናውን በተግባር ማሳየት እንዳለበትም ተናግረዋል።
በስልጠናው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል እና በሥሩ የሚገኙ የ12 ዞኖች ከፍተኛ አመራሮች ተሳትፈዋል።
አዲስ አበባ፤ የካቲት 20/2017(ኢዜአ)፦ የቁልፍ መሰረተ ልማቶች ጥበቃ አዋጅን ሥራ ላይ ለማዋል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስ...
Feb 28, 2025
ደሴ፤ የካቲት 16/2017 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ወሎ ዞን በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት የተሻለ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዓሊ መኮንን ገለ...
Feb 24, 2025
አሶሳ ፤ የካቲት 15/2017(ኢዜአ):- የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ችግር ፈቺ ስራዎችን እንዲያከናውኑ እየተሰራ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 4/2017(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ቀንድ የልማት ትስስርና የኢኮኖሚ ውህደት የመሪነት ሚናዋን እየተወጣች እንደምትገኝ የአፍሪካ ቀንድ...
Feb 12, 2025