አዲስ አበባ፤ ሰኔ 25/2017(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ሀገራት አማራጭ የፋይናንስ አሰራሮችን መጠቀምን የምርጫ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ አድርገው ሊመለከቱት እንደሚገባ የተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን (ዩኤን-ኢሲኤ) ዋና ፀሐፊ ክላቨር ጋቴቴ አመለከቱ።
በስፔን ሲቪያ እየተካሄደ ያለው አራተኛው ዓለም አቀፍ የዘላቂ ልማት ፋይናንስ ኮንፍረንስ ዛሬ ሁለተኛ ቀኑን ይዟል።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አምስት ቀጣናዊ ኮሚሽኖች ከኮንፍረንሱ ጎን ለጎን የዓለም የልማት ፋይናንስ ፈተናዎች እና የመፍትሄ አማራጮችን አስመልክቶ በጋራ ያዘጋጁት ውይይት ተካሄዷል።
የአፍሪካ የኢኮኖሚ ኮሚሽን ዋና ፀሐፊ ክላቫር ጋቴቴ በአፍሪካ በዘላቂ ልማት ፋይናንስ አዳዲስ የመፍትሄ አማራጮች በትግበራ ላይ እንደሚገኙ ገልጸው የዓለም የፋይናንስ ስርዓትም ከነዚህ ለውጦች ጋር ራሱን ማጣጣም እንደሚገባው ተናግረዋል።
የፋይናንስ አሰራሮች የአፍሪካን የልማት ፍላጎቶች የሚያንጸባርቁ መሆን አለባቸው ብለዋል።
ካማሩ ንግግሮች ወደ የሚጨበጡ ውጤቶች መሸጋገር አለብን ያሉት ዋና ፀሐፊው አማራጭ የፋይናንስ ማዕቀፎች የምርጫ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ ናቸው ብለዋል።
አፍሪካ የኢንቨስትመንት አቅም እና የልማት ፍላጎቶች ቢኖሯትም በዓለም የፋይናንስ ስርዓት ምክንያት አሁንም ፍትሃዊ የፋይናንስ አቅርቦት እንዳታገኝ እየገደበች እንደምትገኝ አመክልተዋል።
የአፍሪካ ሀገራት የፋይናንስ ማዕቀፎች ቅድሚያ ከሚሰጣቸው ብሄራዊ የትኩረት መስኮች ጋር በማስተሳሰር፣ በሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች መካከል ያለውን ቅንጅት በማጠናከር እና ግልጽ አሰራር በመፍጠር የረጅም ጊዜ ኢንቨስትመንት ለመሳብ መስራት እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል።
የግሉ ዘርፍ የፋይናንስ አቅምን መጠቀም ይገባል ከሚል መልካም እሳቤ ባለፈ መተማመንን መገንባት፣ ዘላቂ ቅንጅታዊ ትስስር መፍጠር እና ተቋማት እምነት የሚጣልባቸው ማድረግ ያስፈልጋል ነው ያሉት ዋና ፀሐፊው።
የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን፣ የአውሮፓ ኢኮኖሚ ኮሚሽን፣ የላቲን አሜሪካ እና ካሪቢያን ኢኮኖሚ ኮሚሽን፣ የእስያ እና ፓሲፊክ ኢኮኖሚ ኮሚሽን እንዲሁም የምዕራብ እስያ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ኮሚሽን ሁነቱን ያዘጋጁ ቀጣናዊ ተቋማት ናቸው።
ቀጣናዊ ኮሚሽኖቹ በስብሰባው ላይ “Road to Seville” በሚል ባዘጋጁት የጋራ የፖሊሲ መግለጫ ሰነድ ላይ የሀገር ውስጥ ሀብት አሰባሰብ፣ ዘላቂ የእዳ አስተዳደር፣ የዓለም የኢኮኖሚ አስተዳደር፣ ዓለም አቀፍ ትብብር እና የግሉ ዘርፍ ፋይናንስ አስመልክቶ ለፖሊሲ አውጪዎች ይበጃሉ ያሏቸውን ምክረ ሀሳቦች ማቅረባቸውን ኢሴኤ ለኢዜአ በላከው መግለጫ አስታውቋል።
አራተኛው ዓለም አቀፍ የዘላቂ ልማት ፋይናንስ ኮንፍረንስ እስከ ሰኔ 26 ቀን 2017 ዓ.ም ይቆያል::
አዲስ አበባ፤ የካቲት 20/2017(ኢዜአ)፦ የቁልፍ መሰረተ ልማቶች ጥበቃ አዋጅን ሥራ ላይ ለማዋል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስ...
Feb 28, 2025
ደሴ፤ የካቲት 16/2017 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ወሎ ዞን በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት የተሻለ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዓሊ መኮንን ገለ...
Feb 24, 2025
አሶሳ ፤ የካቲት 15/2017(ኢዜአ):- የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ችግር ፈቺ ስራዎችን እንዲያከናውኑ እየተሰራ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 4/2017(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ቀንድ የልማት ትስስርና የኢኮኖሚ ውህደት የመሪነት ሚናዋን እየተወጣች እንደምትገኝ የአፍሪካ ቀንድ...
Feb 12, 2025