🔇Unmute
ሀዋሳ፤ ህዳር 11/2018(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር የዓሣ ልማትና የህብረተሰቡን የአመጋገብ ሥርዓት እያሳደገው መምጣቱን የክልሉ እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ ገለፀ።
በቢሮው የእንስሳት ዝርያ ማሻሻያ ዳይሬክተር ዘሪሁን ጃንጄ እንደገለጹት በክልሉ የሌማት ትሩፋት መርሀግብር ህብረተሰቡ በአነስተኛ ቦታ አትክልቶችን በማልማት የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኝ እያስቻለ ነው።
በልማቱ የሚገኘው ምርት ከራስ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ለማሳደግና ለገበያ መረጋጋት ማገዙን ነው የገለጹት።
በክልሉ በተተገበረው የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር በተለይ አርሶ አደሩ አነስተኛ ኩሬዎችን በማዘጋጀት የዓሣ ሀብት ልማትን እንዲያከናውን የክህሎትና የግብዓት አቅርቦት ድጋፍ መደረጉንም ጠቁመዋል፡፡
በዚህም ባለፈው ዓመት ብቻ 1ሺህ 45 የዓሣ ኩሬዎችን አርሶ አደሮች እንዲያዘጋጁ በማድረግና ከ185ሺህ በላይ የዓሣ ጫጩቶችን በማቅረብ የዓሣ ልማቱ ውጤታማ እንዲሆን መደረጉን ተናግረዋል።

ዘንድሮም ከ1ሺህ 250 በላይ ኩሬዎችን በማዘጋጀት ከ204 ሺህ በላይ የዓሣ ጫጩቶችን ለማሰራጨት ታቅዶ አስካሁን ድረስ ከ62 ሺህ በላይ ጫጩቶች ለአርሶ አደሩ መሰራጨታቸውን ገልጸዋል።
የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ትግበራ በየዓመቱ የዓሣ ምርታማነትን እያሳደገው መሆኑን ጠቁመው በተያዘው ዓመት 5ሺህ 491 ቶን ዓሣ ለመሰበሰብ ታቅዶ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።
መርሀ ግብሩ የአርሶ አደሩን ምርታማነት በማሳደግ የአመጋገብ ሥርዓቱን እንዲያሻሽል ከማድረግ ባለፈ በኢኮኖሚም ተጠቃሚ እያደረገው መሆኑን አመልክተዋል።
በክልሉ የዳራ ቀባዶ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር በሀይሉ በላይ በጓሯቸው በአራት የዓሣ ኩሬዎች ልማቱን እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
የዓሣ ምርታቸውን ከራስ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ ለማቅረብ ጭምር ተግተው በመስራት በዓመት እስከ 10ሺህ ዓሣ እንደሚያመርቱና የዓሣ ጫጩቶችን ለሌሎች አርሶ አደሮች ጭምር በመሸጥ ጥቅም እያገኙ መሆናቸውን አስረድተዋል።
በይርጋዓለም ከተማ የ“ሚቴኒ ሎጲኖ” ዓሣ እርባታ ማህበር ሰብሳቢ ሀብታሙ ሀሪሶ በበኩላቸው በዘጠኝ ኩሬዎች ዓሣ በማልማት በኢኮኖሚ ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናግረዋል።
ለምግብነት የሚውሉና ለርቢ የሚሆኑ የዓሣ ጫጩቶችን እያቀረቡ መሆናቸውን ገልጸው፣ የዓሣ ተጠቃሚዎች ቁጥር እየጨመረ በመምጣቱ ሥራቸውን ለማሳደግ እያገዛቸው መሆኑን አንስተዋል።
አሁን ላይ ለምግብነት የደረሱ ዓሣዎችን ከተማ አስተዳደሩ ባመቻቸላቸው የመሸጫ ቦታዎች ለተጠቃሚዎች ለማቅረብ እየተዘጋጁ መሆናቸውንም አመልክተዋል።
ጅማ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለገበያ መቅረቡን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ቲጃኒ ተማም ተናገሩ...
Apr 24, 2026
ጅግጅጋ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኅብረት ሥራ ማኅበራትን በቴክኖሎጂና ሌሎች መስኮች የማጠናከር ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የሶማሌ ክልል ምክትል ርዕሠ መ...
Apr 22, 2026
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በስንዴ ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካዊያን በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን የአ...
Apr 15, 2026
አዶላ ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በበልግ አዝመራ ከ260 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ...
Apr 9, 2026