
ጎንደር፤ ጥር 29/2017 (ኢዜአ)፡- በጎንደር ከተማ በፌደራል መንግስት እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ፕሮጀክቶች የጥራት ደረጃቸውን በጠበቀ አግባብ በፍጥነት እየተከናወኑ መሆኑን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ አስታወቁ፡፡
የፌደራልና የክልል ከፍተኛ አመራሮች በከተማው እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል።
አመራሮቹ ኮሪደር ልማት፣ የአጼ ፋሲል አብያተ መንግስት እድሳትንና የአዘዞ ጎንደር የኮንክሪት አስፓልት መንገድ ስራና አፈጻጸም ተዘዋውረው ተመልክተዋል፡፡
ሚኒስትሯ በወቅቱ እንደተናገሩት፤ በከተማው እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ፕሮጀክቶች የከተማውን ህዝብ የረጅም ጊዜ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመፍታት ምቹ ሁኔታ የፈጠሩ ናቸው፡፡

"በከተማው ፒያሳ አካባቢ የተከናወነው የኮሪደር ልማት ስራ ለነዋሪዎች ምቹ የመኖሪያ አካባቢን በመፍጠር ጽዱና አረንጓዴ ስፍራዎችን ለማስፋፋት ዕድል የፈጠረ ሞዴል ፕሮጀክት ነው" ብለዋል፡፡
የኮሪደር ልማቱ በጥራትና በፍጥነት በተያዘለት ጊዜ የተጠናቀቀ ከመሆኑም በላይ የከተማው ነዋሪዎች እንዲሁም ተሸከርካሪዎች ነጻ እንቅስቃሴ ማድረግ እንዲችሉ ሆኖ የተገነባ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የአጼ ፋሲል አብያተ መንግስት እድሳትና ጥገና ስራም የቅርሱን ታሪካዊነትና ጥንታዊነት በጠበቀ መንገድ የተካሄደና በዘርፉ የጠለቀ እውቀትና ክህሎት ባላቸው ባለሙያዎች የተካሄደ እንደሆነም አረጋግጠዋል፡፡
"የእድሳትና ጥገና ስራው ቅርሱን ከአደጋ ስጋት መታደግ ያስቻለ ከመሆኑም በላይ የከተማውን የቱሪስት ፍሰት በመጨመርና የቆይታ ጊዜያውን በማራዘም በኩል ፋይዳው የጎላ ነው "ብለዋል፡፡
የነዋሪዎች መሰረታዊ ጥያቄ ሆኖ የቆየው የአዘዞ ጎንደር የኮንክሪት አስፓልት መንገድ ስራ ባለፉት ስድስት ዓመታት መስራት ያልተቻለውን በሶስት ወራት ውስጥ በከፊል ማጠናቀቅ የተቻለበትን ሁኔታ መፍጠር መቻሉን አስረድተዋል፡፡
ይህም የልማት ፕሮጀክቶችን በአጠረ ጊዜና በጥራት ማከናወን እንደሚቻል ማሳያ ከመሆኑም በላይ አዲስ የስራ ባህልን መፍጠርና ዕቅድን የመፈጸም አቅምን ማሳደግ የተቻለበት ፕሮጀክት እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሰጡት አቅጣጫ በከተማው እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ፕሮጀክቶች በጥሩ የአፈጻጸም ደረጃ ላይ የሚገኙና የከተማውን ህዝብ የልማት ተጠቃሚነት በተጨባጭ ያረጋገጡ ናቸው ብለዋል፡፡
"በከተማው በአዲስ የተጀመሩና ነባር የልማት ፕሮጀክቶች የከተማውን እድገትና የቀደመ ስልጣኔ የሚያጎሉ ናቸው" ያሉት ደግሞ የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ናቸው፡፡
በአሁኑ ወቅት የኮሪደር ልማት ስራው የመጀመሪያው ምዕራፍ ተጠናቆ ሁለተኛው ምዕራፍ ወደ ተግባር መሸጋገሩን ጠቁመዋል።
የአጼ ፋሲል አብያተ መንግስት ቅርስ ጥገናና እድሳት ስራም በተመሳሳይ ሁለተኛው ምዕራፍ ተጀምሮ እየተፋጠነ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
በጉብኝት መርሃ ግብሩ ላይ የፌደራል ፣ የክልልና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ የልማት ፕሮጀክቶቹ የስራ ሃላፊዎች ተሳታፊ ሆነዋል፡፡
በሙሴ መለሰ ኢትዮጵያ በአፍሪካ የአቪዬሽን ታሪክ ታይቶ የማይታወቅና በአህጉሪቱ ትልቁ የሆነውን የ12 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር ግዙፍ የኤርፖርት ግንባታ ፕሮጀክት...
Apr 24, 2026
ሆሳዕና ፤ ሚያዝያ 2/2018 (ኢዜአ)፦በሆሳእና፣ ወላይታ ሶዶና ቦንጋ ከተሞች በትንሳዔ በዓል ገበያ በቂ የምርትና የእርድ እንስሳት አቅርቦት መኖሩ ተመለከተ። ...
Apr 12, 2026
አዲስ አበባ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦የጉምሩክ ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ የኢትዮጵያን ዓለም አቀፍ የጉምሩክ አገልግሎት በሚያቀላጥፍ መልኩ እየተዘጋጀ መሆኑን በሕ...
Apr 9, 2026
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፦ የአፋር ሰመራ ሁለተኛ ደረጃ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከል ወደ ሥራ መግባቱ በክልሉ የሚገኘውን ሰፊ የእንስሳት ሀ...
Apr 1, 2026