አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የሚገነቡ ህንጻዎች ዘመኑን የዋጁና ዘላቂ እንዲሆኑ የህንጻ ኮዶችንና ስታንዳርዶችን የማሻሻል ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ።
የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ባለሥልጣን ከከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴርና ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የምክክር መድረክ ዛሬ ተካሂዷል።
በመድረኩ ላይ የህንጻ ኮዶችና ስታንዳርዶች እንዲሁም የሥራ ላይ ደህንነት እና ጤንነት ላይ ትኩረት ያደረጉ ጹሁፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።
የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ዘርፉ በሥራ ዕድል ፈጠራና በኢኮኖሚ እድገቱ ውስጥ የሚጫወተውን ሚና ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግ አዳዲስ አሰራሮችን ከመተግበር ባለፈ ዘመኑ የደረሰበትን ቴክኖሎጂዎች እንዲጠቀም ማድረግ ይገባል።
ለዚህም እያደገ ከመጣው የመሰረተ ልማት ፍላጎትና አቅርቦት ጋር የሚጣጣም የህንጻ ኮድና ስታንዳርዶችን ሥራ ላይ ማዋል ወሳኝ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም ችግሩን የሚቋቋም ዘላቂ ግንባታዎች እንዲኖሩ የሚያስችል ነው ብለዋል።
ለዚህም ሚኒስቴሩ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ከ2007 ዓ.ም ጀምሮ ሥራ ላይ የዋለውን የኢትዮጵያ የህንጻ ኮድና ስታንዳርዶች ማሻሻል የሚያስችል ጥናት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል።
ኮድና ስታንዳርድ መሻሻሉ ከግንባታ ግብዓት፣ ቴክኖሎጂ እና ዘርፉ ከሚፈልገው ክህሎት አኳያ ዘመኑን የዋጁ አሰራሮችን ለመከተል ጉልህ ፋይዳ እንዳለው አብራርተዋል።
የሥራ ላይ ደህንነት እና ጤንነትን በተመለከተ ሕጎችና ደንቦችን ተግባር ላይ ማዋል የሚያስችል የህንጻ አዋጅ መውጣቱንም ገልጸዋል።
የግንባታ ሰራተኞች የሥራ ላይ ደህንነትና ጤንነትን በተመለከተም ሚኒስቴሩ ከባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ጥናቶችን በማካሄድ የምክረ ሀሳቦች ሰነዶች መዘጋጀታቸውን ጠቁመው፤ በጥንቃቄ ጉድለት ሳቢያ በሰራተኞች ላይ የሚደርስን ጉዳት ለመቀነስ፣ አደጋ ሲያጋጥም ተጎጂዎች ፈጣን ህክምና የሚያገኙበት ሥርዓትን ያካተተ መሆኑም ተናግረዋል።
ሚኒስትሯ አክለውም የግንባታ ደህንነትና ጤንነት መረጃ ማሰባሰቢያ ሶፍትዌር መልማቱን ጠቁመዋል።
በአሁኑ ወቅት እየተከሰተ ያለው የርዕደ መሬት ጉዳይ ታሳቢ ያደረጉ ሥራዎች በቀጣይ የሚከናወኑ መሆኑን ገልጸው፤ ለዚህም ሚኒስቴሩ ከባለድርሻ አካላት ባለሙያዎች የሚቀርቡ ምክረ ሀሳቦችን በመቀበል ሥራ ላይ ለማዋል ዝግጁ መሆኑንም አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር መስፍን ነገዎ(ኢ/ር) በበኩላቸው ከዚህ ቀደም 17 የሕንጻ ኮዶች ስራ ላይ እንደነበሩ አስታውሰው፤ አሁን ላይ የተሻሻሉ አሰራሮችን የያዙ ኮዶችን ወደ 30 ከፍ ማድረግ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑም ጠቁመዋል።
ህንጻዎች የተሟላ የስልክ ኔት ወርክ እንዲኖራቸው የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን እንዲጠቀሙ የሚያደርግ አስገዳጅ አሰራር እንደሚዘረጋም አብራርተዋል።
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህርና የኮንስትራክሽን ባለሙያ ኢሳያስ ገብረዮሃንስ (ዶ/ር) ኮዶችና ስታንዳርዶች በኢትዮጵያ በአመዛኙ ከአውሮፓ የተቀዱ መሆናቸውን አስታውሰው ማሻሻያው ኮዶችና ስታንዳርዶቹ ከኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ጋር የተጣጣሙ እንዲሆኑ ለማድረግ ያለመ ነው ብለዋል።
ረጅም ጊዜ ያስቆጠሩ ህንጻዎች አደጋዎችን መቋቋም እንዲችሉ እንዴት መጠናከር አለባቸው የሚለውም በማሻሻያው መካተቱን ጠቁመው የርዕደ መሬት ተጋላጭነት እና የሚወሰዱ የጥንቃቄ እርምጃዎችን ታሳቢ ተደርገው እየተሰሩ መሆኑንም ጠቁመዋል።
አሶሳ፤ የካቲት 20/2017(ኢዜአ):- ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የትውልዱ አሻራና ኩራት ነው ሲሉ የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አብዱልሙህሲን ሐሰን...
Feb 28, 2025
ሚዛን አማን፤የካቲት 20/2017 (ኢዜአ)፦በቤንች ሸኮ ዞን ሚዛን አማን ከተማ በማህበር ተደራጅተው በተለያዩ የሥራ ዘርፎች የተሰማሩ ኢንተርፕራይዞች ውጤታማ በመ...
Feb 28, 2025
አዲስ አበባ፤የካቲት 4 /2017(ኢዜአ)፦ቦንጋ ዩኒቨርሲቲ በግብርናው ዘርፍ እያከናወነ ያለው በምርምር የተደገፈ ስራ ምሳሌ የሚሆን ነው ሲሉ የሕዝብ ተወካዮች ም...
Feb 12, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- የቦንጋ የተቀናጀ የግብርና ግብዓትና ሜካናይዜሽን አገልግሎት ማዕከል መገንባት በክልሉ ለግብርና ስራው መሠረታዊ የሆነ...
Feb 8, 2025