አዲስ አበባ፤ ጥር 29/2017(ኢዜአ)፡- የሁሉም ተቋማት ጥንካሬ የኢትዮጵያ ጥንካሬ በመሆኑ የሚዲያ ተቋማትም በትብብር በመሥራት ጥንካሬያቸውን እንዲያጎለብቱ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሙአዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት አሳሰቡ።
የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን(ኢቢሲ) በዲጂታል ሚዲያው ዘርፍ ባሳየው ጠንካራ የሪፎርም ሥራ ከሌሎች ሚዲያዎች እውቅና ተሰጥቶታል።
ለኢቢሲ በተለይም ለዶትስትሪም ዘርፍ በተሰጠው እውቅና ሥነ-ሥርዓት ላይ ንግግር ያደረጉት ሙአዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት፤ መንግሥታት መልዕክቶችን በድንጋይ ላይ በመጻፍ መረጃ መለዋወጥ የጀመሩት ከአንድ ሺህ ዓመት በፊት እንደነበር ገልጸው፣ በዚህ ሁኔታ የኢትዮጵያ የሚዲያ ታሪክ የአንድ ሺህ ዓመት ታሪክ ያለው ነው ብለዋል።
ከአንድ ሺህ ዓመት በፊት በድንጋይ ላይ መልዕክቶችን ከመለዋወጥ ጀምሮ ዛሬ እስከደረስንበት የዲጂታል ሚዲያ ዘመን የመንግሥት የመረጃ ማዕከልነት ሚና ከፍተኛ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
በተለይ ደግሞ በዚህ መረጃ ከሁሉም አቅጣጫ በሚመነጭበት የዲጂታል ዘመን መንግሥት የመሪነቱን ሚና የበለጠ መጫወት ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን ነው የገለጹት።
ይህንኑ ታሳቢ በማድረግ ሚዲያዎች የሪፎርም ሥራ እንዲያከናውኑ በተሰጠው አቅጣጫ መሠረት ኢቢሲ በዶትስትሪም ዘርፍ አመርቂ ለውጥ በማምጣት ለሌሎች ምሳሌ የሚሆን ሥራ መሥራት ችሏል ብለዋል።
በዚህ ሥራ ውስጥ ከአመራሩ እስከ ጥበቃ እና የፅዳት ሠራተኛ ድረስ የራሳቸውን አስተዋፅኦ ስላበረከቱ ሊመሰገኑ ይገባል ነው ያሉት።
ሌሎች ተቋማትም ኢቢሲ በዲጂታል ሚዲያው ዘርፍ ካከናወነው ውጤታማ የሪፎርም ሥራ ልምድ ሊወስዱ ይገባል ሲሉም መክረዋል።
የሁሉም ኢትዮጵያዊ ዋና ግቡ የሀገሩን ብሔራዊ ጥቅም ማስከበር ነው ያሉት ሙአዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት፤ በዚህ ሂደት ውስጥ የግልም ሆኑ የመንግሥት ሚዲያዎች ከእርስ በርስ ፉክክር ወጥተው በትብብር መሥራት እጅጉን አስፈላጊ መሆኑን አሳስበዋል።
የኢቢሲ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ጌትነት ታደሰ በበኩላቸው፤ ሚዲያዎች ለተቋሙ ሥራ ለሰጡት እውቅና አመስግነው፤ ከመገፋፋት እና ከፉክክር ወጥተው እርስ በርስ መተባበር መጀመራቸው ለሀገር ዕድገት ሚናው የጎላ ነው ብለዋል።
ሚዲያዎችን የማስተባበሩን ሚና ለተጫወቱት ሙአዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረትም ምስጋና ማቅረባቸውን የኢቢሲ መረጃ ያመላክታል።
እንደሚዲያ ተባብሮ መሥራት የበለጠ ውጤታማ እንደሚያደርግ ገልጸው፤ ኢቢሲ በዚህ ረገድ ከሁሉም ሚዲያዎች ጋር ተደጋግፎ ለመሥራት ያለውን ቁርጠኝነት ገልጸዋል።
የኢቢሲ ዶትስትሪም የለውጥ ሂደት እንዲፋጠን ላደረጉ የዘርፉ አመራሮች እና ሠራተኞች እንዲሁም ውጫዊ ድጋፍ ላደረገው የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩትም ምስጋና አቅርበዋል።
አሶሳ፤ የካቲት 20/2017(ኢዜአ):- ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የትውልዱ አሻራና ኩራት ነው ሲሉ የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አብዱልሙህሲን ሐሰን...
Feb 28, 2025
ሚዛን አማን፤የካቲት 20/2017 (ኢዜአ)፦በቤንች ሸኮ ዞን ሚዛን አማን ከተማ በማህበር ተደራጅተው በተለያዩ የሥራ ዘርፎች የተሰማሩ ኢንተርፕራይዞች ውጤታማ በመ...
Feb 28, 2025
አዲስ አበባ፤የካቲት 4 /2017(ኢዜአ)፦ቦንጋ ዩኒቨርሲቲ በግብርናው ዘርፍ እያከናወነ ያለው በምርምር የተደገፈ ስራ ምሳሌ የሚሆን ነው ሲሉ የሕዝብ ተወካዮች ም...
Feb 12, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- የቦንጋ የተቀናጀ የግብርና ግብዓትና ሜካናይዜሽን አገልግሎት ማዕከል መገንባት በክልሉ ለግብርና ስራው መሠረታዊ የሆነ...
Feb 8, 2025