አርባ ምንጭ፤ የካቲት 13/2017(ኢዜአ)፡- አርባ ምንጭ ከተማን በማልማት ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ።
በሚኒስትሯ የተመራና የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎችን ያካተተ ልዑክ በከተማው እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎችን ጎብኝቷል።
ሚኒስትሯ ከጉብኝቱ በኋላ በከተማዋ ባለፉት ስድስት ወራት በተከናወኑ የልማት ሥራዎች አፈጻጸም ላይ ውይይት አድርገዋል፡፡
በዚህም አርባ ምንጭ ከተማን በማልማት ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡
በከተማዋ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ሥራ የከተማዋን ውበት ከመጨመር ባለፈ ለከተማዋ እድገት የራሱን አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።
በሌላ በኩል በከተማ ፕላን፣ በከተሞች ዕድገት እና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎች መልካም መሆናቸውን ሚኒስትሯ ጠቅሰዋል።
በመኖሪያ ቤት አስተዳደርና ቁጥጥር አዋጅ ትግበራ፣ በካዳስተርና በመሠረተ ልማት ዘርፎች እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል ሲሉም አስገንዝበዋል።
የከተማዋን የገቢ አቅም አሟጦ ከመጠቀም አንጻር ውስንነቶች እንዳሉ የጠቀሱት ሚኒስትሯ፣ ያላትን ፀጋ በአግባቡ አልምቶ ለመጠቀም አመራሩ የድርሻውን መወጣት እንዳለበትም አመልክተዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ብርሃኑ ዘውዴ የክልሉ ከተሞች በፕላን እንዲመሩ ከእድገት ደረጃቸው ጋር የተጣጣመ ዕቅድ ተዘጋጅቶ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።
አርባ ምንጭ፣ ሶዶ እና ዲላ ከተሞች ወደ ሪጂዮ ፖሊስ ከተማ ፈርጅ ማደጋቸውን ጠቅሰው፣ ከተሞች ለነዋሪዎቻቸው ምቹና ውብ እንዲሆኑ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ከተሞችን የማዘመንና ለነዋሪዎቻቸው ምቹ የማድረግ ሥራው ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉም ገልጸዋል።
የአርባምንጭ ከተማ ከንቲባ ገዛኸኝ ጋሞ በበኩላቸው፣ በከተማው ባለፉት ሁለት ዓመታት 9 ነጥብ 8 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ከዚህ ውስጥ 5 ነጥብ 7 ኪሎ ሜትሩ ባለፉት ስድስት ወራት የተከናወነ መሆኑንም ነው የተናገሩት።
የከተማዋ ነዋሪዎች የኮሪደር ልማቱ እንዲሳካ ይዞታቸውን ከማንሳት ጀምሮ በገንዘብና በጉልበት ከፍተኛ ድጋፍ ማድረጋቸውንም ተናግረዋል።
ከመንገድ ልማት ጋር በተያያዘም ባለፉት ስድስት ወራት 6 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር የአስፓልት መንገድ ሥራ መከናወኑን ገልጸዋል።
የልዑካን ቡድኑ የኮሪደር ልማትን የዶክተር አመኑ መታሰቢያ ሆስፒታል የሥራ እንቅስቃሴን ጨምሮ ሌሎች የልማት ሥራዎችን ጎብኝቷል።
አሶሳ፤ የካቲት 20/2017(ኢዜአ):- ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የትውልዱ አሻራና ኩራት ነው ሲሉ የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አብዱልሙህሲን ሐሰን...
Feb 28, 2025
ሚዛን አማን፤የካቲት 20/2017 (ኢዜአ)፦በቤንች ሸኮ ዞን ሚዛን አማን ከተማ በማህበር ተደራጅተው በተለያዩ የሥራ ዘርፎች የተሰማሩ ኢንተርፕራይዞች ውጤታማ በመ...
Feb 28, 2025
አዲስ አበባ፤የካቲት 4 /2017(ኢዜአ)፦ቦንጋ ዩኒቨርሲቲ በግብርናው ዘርፍ እያከናወነ ያለው በምርምር የተደገፈ ስራ ምሳሌ የሚሆን ነው ሲሉ የሕዝብ ተወካዮች ም...
Feb 12, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- የቦንጋ የተቀናጀ የግብርና ግብዓትና ሜካናይዜሽን አገልግሎት ማዕከል መገንባት በክልሉ ለግብርና ስራው መሠረታዊ የሆነ...
Feb 8, 2025