
ደሴ ፤የካቲት 20/2017 (ኢዜአ)፡- በደሴ ከተማ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ለህዝብ የተገባውን ቃል በተግባር የሚያረጋግጡ መሆናቸውን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡
ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከደሴ የተወከሉት የፓርላማ አባልና የደሴ ከተማ ምክር ቤት አባላት፣ ከነዋሪዎችና የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች ተወካዮች ጋር ውይይት አድርገዋል።
የመድረኩ ተሳታፊዎችም በተለይም በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎችን በማድነቅ ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል።
አስተያየታቸውን የሰጡ የውይይቱ ተሳታፊዎች እንዳሉት በደሴ ከተማ አስተዳደር የተገነቡት የመሰረተ ልማት አውታሮች መንግስት ለህዝቡ የገባውን ቃል በተግባር ያረጋገጡ ናቸው።
ከውይይት ተሳታፊዎች መካከል አቶ አህመድ ዓሊ፤ በከተማዋ ቀደም ሲል ይሰሩ የነበሩ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ከመጓተትም ባለፈ የጥራት መጓደል የሚስተዋልባቸው እንደነበሩ አስታውሰዋል።
በዚህም ለህዝቡ የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ሆነው መቆየታቸውን አንስተው አሁን ላይ የሚከናወኑ የልማት ስራዎች ግን በጥራት፣ በፍጥነትና የሰዎችን ተጠቃሚነት መሰረት ያደረጉ ስለመሆናቸው አንስተዋል።
መንግስት ለህዝቡ በገባው ቃል መሰረት ተግባራዊ ምላሽ እየሰጠ መሆኑን ተናግረው እኛም የድርሻችንን ለመወጣት ዝግጁ ነን ሲሉ አረጋግጠዋል።
የልማት ስራው እንቅስቃሴ በጥሩ ጎኑ ቢነሳም በአገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ የሚስተዋሉ ችግሮች ግን ውለው ሳያድሩ ሊፈቱ ይገባል ብለዋል።
ሌላው የምክክሩ ተሳታፊ አቶ መላኩ አራጌ፤ የደሴ መናኸሪያ ግንባታን ጨምሮ የመንገድ፣ የካናልና ሌሎችም የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን በማንሳት ለከተማ አስተዳደሩ ምስጋና አቅርበዋል።
የከተማዋን ሰላም በዘላቂነት በማፅናት የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ለማሳካት የሁላችንም እገዛና ትብብር ተጠናክሮ የሚቀጥል ነው ሲሉም ተናግረዋል።
የደሴ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባዔ አገሪቱ እንድሪስ፤ በከተማዋ ለሚከናወኑ ስራዎች መሳካት ለአስፈጻሚው አካል የተጠናከረ ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል።
በዚህ ረገድ የከተማው ነዋሪ ድጋፍና እገዛ በማድረግ ጭምር የልማቱ አጋር መሆኑም ተጨማሪ አቅም ሆኖናል ነው ያሉት።
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የደሴ ከተማ ተወካይ የሆኑት ማህተም ኃይሌ(ዶ/ር)፤ በከተማዋ እየተገነቡ ያሉ የመሰረተ ልማት ስራዎች ህብረተሰቡን በልማትና በመልካም አስተዳደር ተጠቃሚ እያደረጉ መሆኑን በተግባር ተመልክተናል ብለዋል።
ይህም የህዝቡና በየደረጃው ያለው አመራር ትብብርና ለልማት የጋራ አላማ ሰንቆ በመሰራቱ መሆኑን ተናግረዋል።
በተለይም የሰላም ጉዳይ የሁሉም ነገሮች መሰረት መሆኑን አንስተው ሰላምን በማስጠበቅ ልማትን ማጠናቀቅ የሁል ጊዜም ዓላማ አድርጎ መንቀሳቀስ ይገባል ብለዋል።
በዚህ ረገድ የከተማው ምክር ቤት ክትትል፣ ቁጥጥርና ድጋፍ የሚደነቅ መሆኑን ጠቅሰው በቀጣይነት የሁላችንም ሚና ይታከልበታል ሲሉ አረጋግጠዋል።
በመድረኩ በየደረጃው ያሉ አመራሮች፣ የሐይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የደሴ ከተማ ምክር ቤት አባላትና ሌሎችም ተሳትፈዋል፡፡
ሀዋሳ ፤ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፡-በሲዳማ ክልል ዘመናዊና ቀልጣፋ አሰራሮችን በመዘርጋት በርካታ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ወደ ክልሉ በመሳብ የዜጎችን ተጠቃ...
Apr 23, 2026
ድሬዳዋ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ በሀገራዊ ለውጡ ለአምራች ኢንዱስትሪዎች የተሰጠው ትኩረት በአስተዳደሩ የአምራች ኢንዱስትሪዎች ተኪና ወጪ ምርቶችን የማምረ...
Apr 17, 2026
ጅግጅጋ፣መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፡- መንግሥት የከተሞችን እድገትና የነዋሪዎችን ኑሮ ለማሻሻል ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑ ተመለከተ። የኢትዮጵያ ከተሞች የ...
Apr 1, 2026
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የኃይል አቅርቦት ስኬት ቀጣናዊ ትስስርን በማፋጠን የጋራ ብልፅግናን የሚያበስር አህጉራዊ የልማት አጀንዳ ...
Mar 26, 2026