
አዳማ፤ የካቲት 22/2017(ኢዜአ)፦ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ እየተገነባ ያለው የምርምርና ቴክኖሎጂ ፓርክ የምርምር ሥርፀትና የቴክኖሎጂ ሽግግርን እንደሚያፋጥን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለጹ።
ዩኒቨርሲቲው ያስገነባቸውን የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ አስመርቋል።

የኢንዱስትሪ ሚኒስትርና የዩኒቨርሲቲው የቦርድ ሰብሳቢ አቶ መላኩ አለበል በዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ ዛሬ በዩኒቨርሲቲው ለምረቃ የበቁት ፕሮጀክቶች ለመማር ማስተማር ስራው አዎንታዊ ሚና አላቸው።
በተለይ በዩኒቨርሲቲው እየተገነቡ ያሉ የምርምርና የቴክኖሎጂ ፓርክና ዳታ ሴንተር የምርምር ሥርፀትና የቴክኖሎጂ ሽግግርን የሚያፋጥኑ ናቸው ብለዋል።
እንደ ሀገር ኢንዱስትሪውን በዓለም ደረጃ ተወዳዳሪ ለማድረግ፣ አዳዲስ የአመራረት ሂደትን ለመከተልና ቴክኖሎጂን ለማላመድ ወሳኝ መሆናቸውንም ነው ሚኒስትሩ የጠቆሙት።

በትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ኮራ ጡሹኔ በበኩላቸው እንዳሉት ዩኒቨርሲቲዎች ራሳቸውን ማስተዳደር እንዲችሉና ራስ ገዝ እንዲሆኑ እየተሰራ ነው።
ለዚህም አዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ለገቢ ማመንጫነት አስገንብቶ ዛሬ ካስመረቃቸው ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ የሆነውን የቢዝነስ ሴንተር በማሳያነት ጠቅሰዋል።
ምቹ የሥራ አካባቢ መፍጠርና የመምህራን መኖሪያ ቤት ችግርን መፍታት የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የራሱ አስተዋጽኦ እንዳለውም አቶ ኮራ አስገንዘበዋል።
በተለይ የህፃናት ማቆያ በተደራጀ መልኩ ተገንብቶ ለአገልግሎት መብቃቱ ሠራተኞች ሳይቸገሩ ልጆቻቸውን ለማሳደግ ያስችላቸዋል ብለዋል።
አቶ ኮራ እንዳሉት በአዳማ ዩኒቨርሲቲ በግንባታ ላይ ያለው የምርምር ፓርኩ ተቋሙን ከኢንዱስትሪዎች ጋር በማስተሳሰር የፈጠራና የምርምር ግኝቶች ወደ ውጤት እንዲቀየሩ የሚያደርግ ነው።
ይህም ሀገርን በሳይንስ፣ በቴክኖሎጂና በፈጠራ ወደፊት ለማምጣት የሚደረገውን ጥረት ያግዛል ብለዋል።
በዩኒቨርሲቲው ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት ፕሮጀክቶች በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለተጀመሩ የሪፎርም ስራዎች ምሳሌ መሆናቸውንም አቶ ኮራ ጠቅሰዋል።

የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ለሚ ጉታ(ዶ/ር) በበኩላቸው ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት አምስት ፕሮጀክቶች መሆናቸውን ገልጸዋል።
ፕሮጀክቶቹ ዩኒቨርሲቲው የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ፣ ብቁ የሰው ሃይል ለማፍራት እንዲሁም በቴክኖሎጂ፣ በፈጠራና በሳይንስ ዘርፍ የተሰጠውን ተልዕኮ ለማሳካት የሚያስችሉ ናቸው ሲሉም ተናግረዋል።
በተለይ የማህበረሰብ ትምህርት ቤቶቹ የዩኒቨርሲቲው ሠራተኞች ልጆቹ ጥራት ያለው ትምህርት እንዲያገኙ የሚያስችሉ መሆናቸውንም ጠቁመዋል።
እንደ ፕሬዚዳንቱ ገለጻ ዛሬ ለምረቃ የበቁት ፕሮጀክቶች ባለ አራት ወለል የቢዝነስ ማዕከል ህንፃ፣ መኖሪያ ቤቶች፣ የህፃናት ማቆያ ማዕከል፣ 1ኛ እና 2ኛ ደረጃ የማህበረሰብ ትምህርት ቤቶች እንዲሁም የመምህራንና የሠራተኞች የመዝናኛ ማዕከል ናቸው።
ከእነዚህ በተጨማሪ 14 ኪሎ ሜትር የአስፋልት መንገድ ግንባታ፣ የአይሲቲ እና የዳታ ማዕከል፣ ሁለገብ የስብሰባ ማዕከልና ሕንጻዎች እንዲሁም የምርምርና የቴክኖሎጂ ፓርኩ በቅርቡ ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት እንደሚበቁ ተመላክቷል።
ሀዋሳ፣ ነሐሴ20/2018 (ኢዜአ)፡-በሀዋሳ ከተማ የተጀመሩ የሐይቅ ዳርቻ እና የኮሪደር ልማት ሥራዎችን በተያዘላቸው ጊዜ ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ...
Aug 27, 2026
ሐረሪ ፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በሐረሪ ክልል የኢንቨስትመንት ፍቃድ እና መሬት ወስደው ወደ ግንባታና ማምረት ባልገቡ 12 ባለሀብቶች ላይ የኢንቨስትመንት...
Aug 14, 2026
ደሴ፤ነሐሴ 6/2018(ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ173 ሺህ ለሚበልጡ አርሶ አደሮች የሁለተኛ ደረጃ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ደብተር መሰጠ...
Aug 13, 2026
ባሕር ዳር ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገብ መቻሉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር...
Jul 31, 2026