
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2017(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር በቢሊዮን የሚቆጠር የቡና ችግኝ በመትከል ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ጉልህ ሚና እየተወጣች መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ(ዶ/ር) ገለጹ።
የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን ከጣሊያን መንግሥት እና ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር በመተባበር ለኢትዮጵያ ቡና አምራቾች፣ አቅራቢዎች እና በዘርፉ የእሴት ሰንሰለት ላይ የሚሳተፋ አካላትን ማገዝ የሚያስችል ብድር ይፋ ተደርጓል።

የጣሊያን መንግሥት ለዘርፉ የ10 ሚሊዮን ዩሮ የተራዘመ ብድር የፈቀደ ሲሆን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የተገኘውን ብድር የማስተዳደር ኃላፊነትን ይወጣል።
የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ በኢትዮጵያ የቡና ምርት የእሴት ሰንሰለት ከ5 ሚሊዮን በላይ አባወራ እና እማወራ እንዲሁም ከ25 ሚሊዮን በላይ የዘርፉ ተዋንያን ይሳተፉበታል።
ለኢትዮጵያ የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት የቡና ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ወሳኝ መሆኑን ገልጸው፤ ባለፉት አምስት ዓመታት ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል።
የተለያዩ የፖሊሲ ማሻሻያዎች እና ጠንካራ የቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋቱ የአርሶ አደሮች፣ አምራቾችና ሌሎች ተዋንያንን እይታ ቀይሯል ብለዋል፡፡
በበጀት ዓመቱ ስምንት ወራት 257ሺህ ሜትሪክ ቶን ቡና ለውጭ ገበያ በማቅረብ 1 ነጥብ 2 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱንም ገልጸዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በበጀት ዓመቱ መጨረሻ ሁለት ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ገቢ ለማግኘት ያስቀመጡትን አቅጣጫ ማሳካት የሚያስችል ቁመና ላይ እንገኛለን ብለዋል፡፡
በቡና ምርት የእሴት ሰንሰለት ላይ የፋይናንስ ችግር አንዱ ፈተና መሆኑን ጠቅሰው፣ የጣሊያን መንግስት ያደረገው የተራዘመ የብድር አገልግሎት ለዘርፉ ምርታማነት ጉልህ ሚና እንዳለው ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር በተከናወኑ ተግባራት የሀገሪቱን የደን ሽፋን መጨመር መቻሏን ገልጸው፣ በመርሃ ግብሩ በቢሊዮን የሚቆጠር የቡና ችግኝ መትከሏንም ጠቅሰዋል።
በዚህም የቡና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ኢኮኖሚውን ከመደገፍ ባለፈ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ወሳኝ ሚና እያበረከተች መሆኑን ማሳያ ነው ብለዋል።

የጣሊያን የልማት ትብብር ኤጀንሲ ዳይሬክተር ማይክል ሞራና የጣሊያን መንግስት የኢትዮጵያን የቡና ልማት የእሴት ሰንሰለት ለማገዝ ያሳየው ፍላጎት ሀገራቱ ለጋራ ልማት ያላቸውን ቁርጠኝነት የሚገልጽ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
ለኢትዮጵያ የቡና ልማት ከኢኮኖሚ ባሻገር ሀገራዊ መገለጫና መለያ መሆኑን ጠቅሰው፣ የጣሊያን መንግስት ለዘርፋ እሴት ሰንሰለት መሳለጥ ድጋፍ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዝዳንት አቤ ሳኖ በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ ጥራት ያለው ቡና ማምረት የሚያስችል ምቹ ሁኔታ መኖሩን ገልጸው፤ የዘርፉን የእሴት ሰንሰለት ለማጠናከር ትብብሩ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የቡናውን ዘርፍ ለረጅም ዓመታት ከሀገር ውስጥ ገቢ በሚገኝ ሀብት ሲያግዝ እንደነበር የተናገሩት ፕሬዝዳንቱ፤ ከጣሊያን መንግሥት የተገኘው የተራዘመ ብድር ተጨማሪ አቅም የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ሰመሪታ ሰዋሰው የፋይናንስ ችግር በቡና ልማት ዘርፍ ለተሳተፉ የዘርፉ ተዋንያን ፈተና መሆኑን አንስተዋል፡፡
የጣሊያን መንግሥት ያቀረበው የብድር ስምምነት ለአምራቾችና ላኪዎች ተመጣጣኝ የብድር አገልግሎት በመስጠት ምርትና ምርታማነት ማሳደግ ያስችላል ብለዋል፡፡
ሀዋሳ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ ሀዋሳ ከተማን በማልማት የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት ማዕከልነቷን ይበልጥ ለማሳደግ የሚከናወኑ የልማት ተግባራት ተጠናክረው እንደሚ...
Jun 14, 2026
ጋምቤላ፤ ሰኔ 3/2018(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በዘንድሮው የመኸር እርሻ ለማልማት ከታቀደው ውስጥ ከ72 በመቶ በላይ የሚሆነው መሬት በዘር መሸፈኑን የክልሉ ...
Jun 11, 2026
ደብረ ማርቆስ ፤ግንቦት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በተከናወነ የንብ ማነብ ስራ ወደ 3 ሚሊዮን ኪሎ ግራም የሚጠጋ የማ...
Jun 4, 2026
ዲላ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፡-ከ40 በላይ የንግድ ተቋማትና አጋር አካላት ተሳትፈውበት በዲላ ከተማ የተዘጋጀው "ቡኖ - ማላ" ኤክስፖ ምርቶችን እና የኢ...
May 25, 2026