ሚዛን አማን ፤መጋቢት 24/2017 (ኢዜአ):-በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብርን ውጤታማ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን የክልሉ የግብርና ቢሮ አስታወቀ።
ዛሬ በሚዛን አማን ከተማ በዶሮ መንደር ለተደራጁ ሴቶች ዘመናዊ የዶሮ ቤት የማስረከብ ሥነ ሥርዓት ተካሄዷል።
የክልሉ ግብርና ቢሮ ጽሕፈት ቤት ኃላፊና አማካሪ አቶ ዮሐንስ መላኩ እንዳሉት በከተሞች የሚታየውን የእንቁላል ምርት እጥረት ለመቅረፍ በዶሮ እርባታ የተደራጁ መንደሮችን ሞዴል ለማድረግ እየተሠራ ነው።
በዘንድሮ በጀት ዓመት ከ5 ነጥብ 6 ሚሊዮን በሚበልጥ በጀት 600 ዘመናዊ የዶሮ ቤቶችን በሚዛን፣ በቴፒ፣ በቦንጋና በታርጫ ከተሞች በዶሮ መንደር ለተደራጁ ግለሰቦች ይሠራጫል ብለዋል።
ከነዚህም ውስጥ በሚዛን አማን ከተማ 30 ሆነው ለተደራጁ ሞዴል የዶሮ አርቢዎች ሥልጠና በመስጠት ዘመናዊ የዶሮ ቤት ማስረከባቸውን ገልጸዋል።
በሌማት ትሩፋት የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ እና የእንስሳት ሀብት ውጤታማነት ምጣኔን ከፍ የማድረግ ግብን ለማሳካት በሌሎችም ዘርፎች መሰል ድጋፎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አስገንዝበዋል።
በክልሉ ከ500 በላይ የዶሮ መንደሮች በከተማና በገጠር መኖራቸውን አቶ ዮሐንስ ጠቅሰዋል።
የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ግሩም ተማም በበኩላቸው በሌማት ትሩፋት ሥራ እየተገኘ ያለውን እንቁላል ኅብረተሰቡ በቀላሉ ማግኘት እንዲችል የመሸጫ ቦታ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።
ክልሉ ዛሬ ያደረገው ድጋፍ ተግባሩን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ የሚያስችል ነው ያሉት ከንቲባው እንደ ከተማ አስተዳደሩ የዶሮ መንደሩን ውጤታማ ለማድረግ ክትትልና ድጋፍ እናደርገለን ብለዋል።
የዶሮ ቤት ድጋፍ ከተደረጋላቸው ሴቶች መካከል ወይዘሮ ፍጹም ሰዒድ በተረከቡት የዶሮ ቤት 50 ዶሮዎችን ለማርባት መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።
አሁን ላይ ካላቸው 10 ዶሮዎች የሚያገኙትን እንቁላል ለቤት ቀለብ እንደሚጠቀሙ ገልጸው በቀጣይም አስፋፍተው ወደ ገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ለመሆን ማቀዳቸውን ገልጸዋል።
የተሰጣቸው ዘመናዊ የዶሮ ቤት ዶሮዎች በአውሬ እንዳይበሉ ከማድረግ ባሻገር የራሱ የሆነ መመገቢያና እንቁላል መጣያ ያለው በመሆኑ ምቹ ነው ያሉት ደግሞ ወይዘሮ ትዝታ ወዛብ ናቸው።
መንግሥት እያደረገ ባለው ድጋፍ ተበረታተው ራሳቸውን እና ቤተሰቦቻቸውን ለመለወጥ የሚያስችል ሥራ እንደሚሠሩ ተናግረዋል።
ከዶሮ ቤት ማስረከብ ሥነ ሥርዓት በኋላ በሚዛን አማን ከተማ እንቁላል በማምረት ሥራ ላይ የተሰማሩ ወጣቶች የሥራ እንቅስቃሴ ምልከታ ተደርጓል።
አሶሳ፤ የካቲት 20/2017(ኢዜአ):- ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የትውልዱ አሻራና ኩራት ነው ሲሉ የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አብዱልሙህሲን ሐሰን...
Feb 28, 2025
ሚዛን አማን፤የካቲት 20/2017 (ኢዜአ)፦በቤንች ሸኮ ዞን ሚዛን አማን ከተማ በማህበር ተደራጅተው በተለያዩ የሥራ ዘርፎች የተሰማሩ ኢንተርፕራይዞች ውጤታማ በመ...
Feb 28, 2025
አዲስ አበባ፤የካቲት 4 /2017(ኢዜአ)፦ቦንጋ ዩኒቨርሲቲ በግብርናው ዘርፍ እያከናወነ ያለው በምርምር የተደገፈ ስራ ምሳሌ የሚሆን ነው ሲሉ የሕዝብ ተወካዮች ም...
Feb 12, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- የቦንጋ የተቀናጀ የግብርና ግብዓትና ሜካናይዜሽን አገልግሎት ማዕከል መገንባት በክልሉ ለግብርና ስራው መሠረታዊ የሆነ...
Feb 8, 2025