
ወልቂጤ፤ ግንቦት 3/2017(ኢዜአ)፦ የሀገር የትኩረት አቅጣጫዎች እንዲሁም የቴክኖሎጂ ፈጠራና ሽግግር ላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ገለጸ።
የማህበረሰቡን ችግር የሚፈቱ ተግባር ተኮር የጥናትና ምርምር ሥራዎች ላይም እንዲሁ በማተኮር ውጤታማ ሥራ እያከናወነ መሆኑን አስታውቋል።
በዩኒቨርሲቲው 6ኛው ዙር ሀገር አቀፍ የጥናትና ምርምር ኮንፍረንስ "እውቀት መር ኢኮኖሚ ለድህነት ቅነሳና ለማህበራዊ ዋስትና'' በሚል መሪ ሀሳብ ተካሂዷል።

የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ፋሪስ ደሊል(ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንደገለጹት ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ሥራው ጎን ለጎን የአካባቢውን ማህበረሰብ ችግሮች የሚፈቱ ተግባር ተኮር የምርምርና ጥናት ሥራዎችን ያከናውናል።
በተለይም የህብረተሰቡን ኑሮ የሚያሻሽሉ የግብርና፣ ትምህርትና ጤና ዘርፍ ውጤታማና ዘላቂ መፍትሄ የሚያመጡ የጥናትና ምርምር ስራዎች በማከናወን ተግባር ላይ እንዲወሉ ለሚመለከተው አካል ማቅረቡን ተናግረዋል።
በተጨማሪም የሀገር የትኩረት አቅጣጫዎች እንዲሁም የቴክኖሎጂ ፈጠራና ሽግግር ላይ ትኩረት አድርጎ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
ዩኒቨርሲቲው በቴክኖሎጂና ፈጠራ ዘርፍ የእንሰት መፋቂያ ማሽን ሰርቶ በማህበር ለተደራጁ ወጣቶች ሽግግር ማድረጉን ገልጸው፣ ማሽኑ የእናቶችን ጊዜ፣ ጉልበትና ገንዘብ ቆጥቧል ብለዋል።

ከጥናት ባለፈ ወደ ተግባር የተቀየሩ 19 የምርምር ውጤቶች እና 57 ፕሮጀክቶች ወደ ማህበረሰቡ ተደራሽ መደረጋቸውን የገለፁት ደግሞ የዩኒቨርስቲው የምርምር እና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት ዮሐንስ ገብሩ(ዶ/ር) ናቸው።
በእንስሳት ዝርያ ማሻሻልና በአሳ ልማት ዘርፍ የተለያዩ ጥናቶችን ከማድረግ ባሻገር ወደ ተግባር በመቀየር ለተጠቃሚው ማህበረሰብ ተደራሽ እየተደረጉ መሆኑንም ጠቅስዋል።
ከኮንፍረንሱ ተሳታፊዎች መካከል በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ ተጠባባቂ ዲንና የኢኮኖሚክስ መምህሩ አጥናፉ ገብረመስቀል(ዶ/ር) እንዳሉት የጥናትና ምርምር ሥራዎች ለድህነት ቅነሳና ቀጣይነት ላለው የሀገር እድገት ሚናቸው የጎላ ነው።
ለእድገት ጠቀሜታ ያላቸውን ሀገር በቀል እውቀቶች ለኢኮኖሚ ግንባታ ለመጠቀምና ለማሸጋገር ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቅንጅት ሊሰሩ እንደሚገባም ገልጸዋል።
የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እንዲሁም በጤና ላይ የሚከናወኑ የጥናትና ምርምር ሥራዎች ተግባር ተኮር መሆን እንዳለባቸውም ጠቁመዋል።
በኮንፍረንሱ 26 የጥናትና ምርምር ሥራዎች የቀረቡ ሲሆን ወደ ተግባር የተቀየሩ የምርምር ውጤቶችም ተጎብኝተዋል።
ለሦስት ቀናት በተካሄደው የምርምር ኮንፍረንስ ላይ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፖሊሲ ጥናትና ምርምር ተቋም ዳይሬክተር አክመል መሐመድ(ዶ/ር)፣ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተውጣጡ ጥናት አቅራቢዎች እና የዩኒቨርሲቲው አመራሮችና መምህራን ተገኝተዋል።
ሀዋሳ፣ ነሐሴ20/2018 (ኢዜአ)፡-በሀዋሳ ከተማ የተጀመሩ የሐይቅ ዳርቻ እና የኮሪደር ልማት ሥራዎችን በተያዘላቸው ጊዜ ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ...
Aug 27, 2026
ሐረሪ ፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በሐረሪ ክልል የኢንቨስትመንት ፍቃድ እና መሬት ወስደው ወደ ግንባታና ማምረት ባልገቡ 12 ባለሀብቶች ላይ የኢንቨስትመንት...
Aug 14, 2026
ደሴ፤ነሐሴ 6/2018(ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ173 ሺህ ለሚበልጡ አርሶ አደሮች የሁለተኛ ደረጃ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ደብተር መሰጠ...
Aug 13, 2026
ባሕር ዳር ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገብ መቻሉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር...
Jul 31, 2026