
ዲላ፤ ግንቦት 6/2017(ኢዜአ)፦ በሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር የተቀናጀ የግብርና ልማት ሥራ ማከናወናቸው ተጠቃሚነታቸውን እያሳደገው መሆኑን በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የጌዴኦ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ።
በክልሉ በየአካባቢው ያለውን ጸጋና ሃብት ታሳቢ ያደረገ የሌማት ትሩፋት ትግበራን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማሳደግ መቻሉም ተመላክቷል።
በጌዴኦ ዞን ገደብ ወረዳ የሚኖሩት አርሶ አደር ቦጋለ ዊሲ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በአካባቢያቸው ካሉ 20 አርሶ አደሮች ጋር ተቀናጅተው "ላክቻ" የተሰኘ የማር መንደር መስርተው ወደ ምርት ገብተዋል።
በመንደሩ 551 ዘመናዊና ባህላዊ የንብ ቀፎዎች እንዳሉና በማር ምርት ውጤታማ መሆናቸውን አንስተዋል።
በተለይ ንቦች በአካባቢው እንዲቀስሙ የተሻሻሉ የቡና ዝሪያዎችን ጎን ለጎን በማልማት የተቀናጀ የግብርና ልማት ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውንም ተናግረዋል።
በዚህም የቡና ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ አርሶ አደሮቹ በዓመት 30 ኪሎ ግራም የተጣራ ማር ለገበያ እንደሚያቀርቡ ገልጸዋል።
የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር የተሰማሩበትን የንብ ማነብ ሥራን ለማጠናከር እንዳስቻላቸው ገልጸው፣ በልማቱ ውጤታማ እንዲሆኑ መንግስት በተለያየ መንገድ እያደረገላቸው ያለው ድጋፍ እንዲጠናከር ጠይቀዋል።
የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በሀገር በቀል የጥላ ዛፎች ውስጥ ማልማታቸው ለማር ምርት የሚሆን የእጽዋት ስብጥር እንደፈጠረላቸው የገለጹት ደግሞ ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ወይዘሮ መስከረም ዳዬ ናቸው።
በዘመናዊ የንብ ቀፎዎች ታግዘው እያከናወኑት ባለው የንብ ማነብ ሥራ ከቤተሰብ ፍጆታ ባለፈ ጥራቱን የጠበቀ ማር ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በዞኑ የቡሌ ከተማ ነዋሪ አርሶ አደር ዳዊት ተፈራ በበኩላቸው የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር የተቀናጀ የግብርና ልማት በማከናወን ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እያገዛቸው መሆኑንም ተናግረዋል።
በዘርፉ በመንግስት የግብዓትና የሙያ ድጋፍ ማግኘታቸውን ጠቁመው በወተት፣ በንብ ማነብና በበግ እርባታ ሥራ መሰማራታቸውን ገልጸዋል።
በዚህም ሲያከናውኑት የነበረው የንብ ማነብ ሥራ ወደ ዘመናዊ የንብ ማነብ ሥራ መተካት እንዳስቻላቸው ተናግረዋል።
የተቀናጀ የግብርና ሥራ ማከናወናቸው ንቦች የሚቀስሙትን በቅርበት እንዲያገኙ በማድረግ የማር ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ የእንስሳት መኖ በተሻለ ሁኔታ ማግኘታቸውን ጠቁመዋል።
የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትልና የእንስሳት ዝርያና መኖ ልማት ዘርፍ ሃላፊ አባይነህ ከዳ(ዶ/ር) በክልሉ የየአካባቢውን ጸጋና ሃብት ታሳቢ ያደረገ የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር እየተከናወነ መሆኑንና በዚህም የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል ብለዋል።
በተለይ የማር፣ የዶሮ፣ የሥጋና የወተት መንደሮችን ከመመስረት ባለፈ ጌዴኦን ጨምሮ የጥምር ግብርና ባለባቸው ዞኖች አርሶ አደሩ በንብ ማነብ ሥራ በስፋት እንዲሳተፍ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል።
ባለፉት አስር ወራት ብቻ ከ151ሺህ 400 በላይ ዘመናዊና ባህላዊ የንብ ቀፎዎች ለአርሶ አደሩ ተሰራጭተዋል ብለዋል።
በዚህ ጊዜ ውስጥም ከ14ሺህ 500 ቶን በላይ የማር ምርት ለገበያ መቅረቡን ተናግረዋል።
ይህም አምና በዓመቱ ከተገኘው የማር ምርት ብልጫ እንዳለው ጠቅሰው በወተት፣ በዶሮ ሥጋ ምርቶችም ተጨባጭ ውጤት እየተገኘ መምጣቱን ገልጸዋል።
ሀዋሳ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ ሀዋሳ ከተማን በማልማት የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት ማዕከልነቷን ይበልጥ ለማሳደግ የሚከናወኑ የልማት ተግባራት ተጠናክረው እንደሚ...
Jun 14, 2026
ጋምቤላ፤ ሰኔ 3/2018(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በዘንድሮው የመኸር እርሻ ለማልማት ከታቀደው ውስጥ ከ72 በመቶ በላይ የሚሆነው መሬት በዘር መሸፈኑን የክልሉ ...
Jun 11, 2026
ደብረ ማርቆስ ፤ግንቦት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በተከናወነ የንብ ማነብ ስራ ወደ 3 ሚሊዮን ኪሎ ግራም የሚጠጋ የማ...
Jun 4, 2026
ዲላ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፡-ከ40 በላይ የንግድ ተቋማትና አጋር አካላት ተሳትፈውበት በዲላ ከተማ የተዘጋጀው "ቡኖ - ማላ" ኤክስፖ ምርቶችን እና የኢ...
May 25, 2026