
አርባ ምንጭ፤ ግንቦት 27/2017(ኢዜአ)፦ የመንግስትና የህዝብ ውስን ሀብት ለታለመለት ዓላማ እንዲውል የምክር ቤት አባላት የሚያከናውኑትን የቁጥጥርና የክትትል ሥራ ማጠናከር እንዳለባቸው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ-ጉባኤ ሎሚ በዶ ገለጹ።
ምክትል አፈ-ጉባኤዋ ይህን ያሉት በአርባ ምንጭ ከተማ እየተካሄደ ባለው 23ኛው የፌዴራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት የዋና ኦዲተሮች እና ባለድርሻ አካላት ዓመታዊ ጉባኤ ላይ ተገኝተው ነው።
በየደረጃው ባሉ የመንግስት ተቋማት ብልሹ አሠራር፣ ህገ-ወጥ ተግባር እና ስልጣንና ሃላፊነትን ያለአግባብ የመጠቀም ዝንባሌ እንደሚስተዋል ጠቅሰው፣ ይህም በሀገራዊ አድገት ላይ ጫና እያሳደረ ይገኛል ብለዋል።

በየደረጃው ያሉ የምክር ቤት አባላትና አፈ ጉባኤዎች በጀት ከማጽደቅ ባለፈ የህዝብና የመንግስት ውስን ሀብት ለታለመለት ዓላማ እንዲውል የሚያከናውኑትን የክትትልና የቁጥጥር ሥራ ማጠናከር እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል።
በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ቋሚ ኮሚቴ ከፌደራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ጋር በቅርበት በመስራት የኦዲት ግኝቶችን ከመፈተሽ ባለፈ በአጥፊዎች ላይ ህጋዊና አስተማሪ እርምጃ እንዲወሰድ እየሠራ መሆኑንም ተናግረዋል።
የመንግስት ተቋማትና ሌሎች ድርጅቶችን ከብልሹ አሠራር ለማጽዳት የኦዲት ተቋማት ሚና ጉልህ መሆኑን ጠቅሰው፣ ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤቱ ከተቋማዊ ሥራ ባሻገር ለሀገራዊ የኦዲት አሠራር ውጤታማነት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል ብለዋል።
ህገወጥነትና ብልሹ አሠራሮችን ከማጋለጥ ባለፈ በአጥፊዎች ላይ እርምጃ በመውሰድ የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ምክትል አፈ ጉባኤዋ ጠቁመዋል።

የፌደራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ በበኩላቸው በየደረጃው ከሚገኙ የህዝብ ተወካዮች ጋር በመቀናጀት የሀገርና የህዝብ ውስን ሀብትን ከምዝበራ ለመታደግ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።
ተቋማቸው በክልሎችና በከተሞች አስተዳደር ካሉ ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤቶች ጋር ጠንካራ ተዋረዳዊ የሥራ ግንኙነት እንዳለውም ጠቅሰዋል።
የሀገሪቱን የኦዲት ሥራ ይበልጥ ከፍ ለማድረግ ለኦዲተሮች በዓለም አቀፍ ስታንዳርድ መሠረት አቅም የመገንባት ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።
በመንግስት ከሚሰሩ ሥራዎች በተጨማሪ ህዝብም ክፍተቶችን ሲያይ ፈጥኖ ጥቆማ በመስጠት የበኩሉን እንዲወጣ ጠይቀዋል።
ለሦስት ቀናት በተዘጋጀው መድረክ የፌደራል፣ የክልል እና የከተሞች ምክር ቤት አፈ ጉባኤዎች፣ የቋሚ ኮሚቴዎች አባላትና ዋና ኦዲተሮች እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ይገኛሉ።
ሀዋሳ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ ሀዋሳ ከተማን በማልማት የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት ማዕከልነቷን ይበልጥ ለማሳደግ የሚከናወኑ የልማት ተግባራት ተጠናክረው እንደሚ...
Jun 14, 2026
ጋምቤላ፤ ሰኔ 3/2018(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በዘንድሮው የመኸር እርሻ ለማልማት ከታቀደው ውስጥ ከ72 በመቶ በላይ የሚሆነው መሬት በዘር መሸፈኑን የክልሉ ...
Jun 11, 2026
ደብረ ማርቆስ ፤ግንቦት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በተከናወነ የንብ ማነብ ስራ ወደ 3 ሚሊዮን ኪሎ ግራም የሚጠጋ የማ...
Jun 4, 2026
ዲላ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፡-ከ40 በላይ የንግድ ተቋማትና አጋር አካላት ተሳትፈውበት በዲላ ከተማ የተዘጋጀው "ቡኖ - ማላ" ኤክስፖ ምርቶችን እና የኢ...
May 25, 2026