
አዲስ አበባ፤ሰኔ 3/2017(ኢዜአ)፦የሲቪል ሰርቪስ ሰራተኛው ከተማዋን የሚመጥን ከሌብነት የጸዳ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት የመስጠት ኃላፊነቱን በአግባቡ መወጣት እንዳለበት የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡
''ብቃት ያለው ሲቪል ሰርቪስ ለኢትዮጵያ ብልጽግና '' በሚል መሪ ሀሳብ ከወረዳ ጀምሮ በየደረጃው ባሉ የሲቪል ሰርቪስ ሰራተኞች ሲካሄድ የነበረው የውይይት መድረክ ዛሬ ተጠናቋል።

የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማጠቃለያ መርሐ-ግብሩ ላይ ተገኝተው ከሲቪል ሰርቪስ ሰራተኞች ለተነሳላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በዚሁ ጊዜ መንግስት ከአገራዊ ለውጡ በኋላ የሲቪል ሰርቪስ ሰራተኞችን ጨምሮ የዜጎችን ኑሮ ለማሻሻል የተለያዩ ርምጃዎች መውሰዱን አብራርተዋል።
በተለይም በከተማዋ የሚነሱ የልማትና የፍትሃዊነት ጥያቄዎችን በዘላቂነት ለመመለስ የአስር ዓመት ግብና ስትራቴጂ በመንደፍ የተለያዩ ተግባራት መከናወኑንም ነው ያነሱት።
በዚህም ባለፉት አምስት ዓመታት ከህብረተሰቡ ከ25 ቢሊዮን ብር በላይ በማሰባሰብ ሰው ተኮር የልማት ስራዎችን ማከናወኑን አመልክተዋል።
በሰው ተኮር ፕሮጀክቶች በተሰሩ ስራዎችን በከተማዋ ማህበራዊ ፍትህን ማረጋገጥ መቻሉን ገልጸው፥ ለስኬቱ መገኘት ሲቪል ሰርቪስ ሰራተኛው የማይተካ ሚና አለው ብለዋል።
የሲቪል ሰርቪስ ሰራተኞች ከሌብነት የጸዳ፣ ቀልጣፋና ብቃት ያለው አገልግሎት በመስጠት ሀገራዊ ሃላፊነታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።
በውይይቱ የተሳተፉ የሲቪል ሰርቪስ ሰራተኞች በበኩላቸው፣ ከሀገራዊ ለውጡ በኋላ በከተማዋ የተከናወኑ የልማት ስራዎችን አድንቀዋል።
ይሁንና ከኑሮ ውድነት፣ ከቤት ኪራይ መጨመር፣ ከፍትሃዊ የስራ ምደባና የደረጃ ዕድገት ጋር ተያይዞ ያልተፈቱ ችግሮች መኖራቸውን ነው ያነሱት።
ከተማ አስተዳደሩ በተለይም የቤት ችግርን ለመፍታት የጀመራቸው ስራዎች እንዲፋጠኑም ጠይቀዋል።

የአዲስ አበባ ፐብሊክ ሰርቪስ ቢሮ ሃላፊ ጀማሉ ጀንበር (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ እንደ ከተማ የሲቪል ሰርቪሱን አገልግሎት አሰጣጥ ለማሻሻል የህግ ማዕቀፎቸን ከማሻሻል ጀምሮ የተለያዩ የሪፎርም ሥራዎች ተከናውነዋል ብለዋል።
የደረጃ ዕድገትና የሥራ ምደባ ብቃት ላይ ብቻ ተመሰርቶ እንደሚከናወንና ህዝቡን በቅንነት በታማኝነትና በብቃት ለሚያገለግል ሰራተኛ ወጥ የሆነ የማትጊያ ስርዓት ለመዘርጋት የተጀመሩ ሥራዎች መኖራቸውን አብራርተዋል።

የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ ጃንጥራር አባይ፣ በከተማዋ የኑሮ ውድነትን ማቃለል የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አብራርተዋል።
የገበያ ማዕከላትን ለሸማቹ ተደራሽ ከማድረግ ባለፈ ምርቶች በገበያ ማዕከላትና በሸማች ማህበራት በኩል በተመጣጣኝ ዋጋ በስፋት እንዲቀርቡ የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል።
ሲቪል ሰርቪስ ሰራተኛው የከተማዋን ዕድገት የሚመጥን ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት የተገልጋዩን እርካታ ሊጨምር እንደሚገባም አሳስበዋል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማጠቃለያ መልዕክታቸው የአገልጋይነት ስሜት መላበስ ከአስተሳሰብ እንደሚጀምር ገልጸው፤ ጥራት ያለው አገልግሎት በመስጠት የህዝቡን እንግልት መቀነስና እርካታውን መጨመር ለነገ የማይባል ስራ ነው ብለዋል።
የአገልግሎት ቅልጥፍናን ለመጨመር በሲቪል ሰርቪስ ተቋማት በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራር ለመዘርጋት የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አፅንኦት ሰጥተዋል።
የሲቪል ሰርቪስ ሰራተኞችን ተጠቃሚ ለማድረግ የተለያዩ የድጎማ ስርዓቶች እየተተገበሩ መሆኑን ጠቅሰዋል።
በቀጣይም ሰራተኞች ለሚያነሷቸው ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ ምላሽ የመስጠት ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።
ሀዋሳ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ ሀዋሳ ከተማን በማልማት የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት ማዕከልነቷን ይበልጥ ለማሳደግ የሚከናወኑ የልማት ተግባራት ተጠናክረው እንደሚ...
Jun 14, 2026
ጋምቤላ፤ ሰኔ 3/2018(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በዘንድሮው የመኸር እርሻ ለማልማት ከታቀደው ውስጥ ከ72 በመቶ በላይ የሚሆነው መሬት በዘር መሸፈኑን የክልሉ ...
Jun 11, 2026
ደብረ ማርቆስ ፤ግንቦት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በተከናወነ የንብ ማነብ ስራ ወደ 3 ሚሊዮን ኪሎ ግራም የሚጠጋ የማ...
Jun 4, 2026
ዲላ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፡-ከ40 በላይ የንግድ ተቋማትና አጋር አካላት ተሳትፈውበት በዲላ ከተማ የተዘጋጀው "ቡኖ - ማላ" ኤክስፖ ምርቶችን እና የኢ...
May 25, 2026