
ሐረር፣ሚያዚያ 14/2017(ኢዜአ)፦በሐረሪ ክልል ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር በተከናወኑ ስራዎች አበረታች ለውጦች መመዝገባቸው ተገለፀ።
በክልሉ እየተካሄደ በሚገኘው የዘጠኝ ወራት የስራ አፈፃፀም ግምገማ መድረክ የክልሉ የግብርና ልማት ቢሮና የክልሉ ባህል፣ ቅርስና ቱሪዝም ቢሮ ሪፖርቶች ቀርበዋል።
ምክትል ርዕሰ መስተደድር እና የክልሉ ግብርና ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሮዛ ዑመር በወቅቱ እንዳሉት፤ በክልሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በዘርፉ የተከናወኑ ተግባራት በገጠርና በከተማ የሚገኘውን ህብረተሰብ ከተረጂነት ወደ ምርታማነት እያሸጋገሩ ይገኛሉ።
በሌማት ትሩፋት፣በከተማ ግብርና፣በመስኖ ልማት፣በመኸርና በበልግ ወራት የተሰሩ ስራዎች በሁለት ወረዳዎች የሚገኙ ከ1 ሺህ 800 በላይ ቤተሰቦችን ከተረጂነት ወደ ምርታማነት እንዲሸጋገሩ ማድረጉን አንስተዋል።
በዘንድሮ በጋ ወራት 4 ሺህ 600 ሄክታር መሬትን በመስኖ በማልማት ከአንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ የአዝርዕት፣ የፍራፍሬና አትክልት ምርቶች ሊሰበሰብ መቻሉን ገልጸዋል።
በተለይ በገጠርና በከተማ በዓመት ሶስት ጊዜ የማምረት ባህልን ለማጎልበት የተሰሩ ህዝባዊ ንቅናቄዎች የአስተሳሰብ ለውጥ እያመጡ መሆኑን አመልክተዋል።
ለአብነትም ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ማሽላን በመስኖ ማምረት እንደሚቻል በሰርቶ ማሳያ በማሳየት በክልሉ ገጠር አካባቢ የሚኖረው ህብረተሰብ ስራውን ወደ ተግባር ለመቀየር ዝግጁ እንዲሆን መደረጉንም አስረድተዋል።
ባለፉት ዘጠኝ ወራት የተሰሩ ስራዎች ምርትና ምርታማነት እንዲጨምርና ከተረጂነት መላቀቅ እንደሚቻል ያሳዩ ተጨባጭ ውጤቶች የተመዘገበባቸው መሆናቸውን ወይዘሮ ሮዛ ተናግረዋል።
በበጋ ወራት የተመረቱ የቲማቲም፣ የቃሪያ እና የሽንኩርት ምርቶች ለቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ቀርበው ዋጋ በማረጋጋት ረገድ ዓይነተኛ ሚና መጫወታቸውን ገልፀዋል።
በቀሪ በጀት ወራት የተገኙ ውጤቶችን ከማጠናከር በተጨማሪ ለቀጣይ የአረንጓዴ አሻራ ዘመቻ የችግኝ ዝግጅት ስራን የማጠናቀቅ እና የማዳበሪያ አቅርቦትን የማፋጠን ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል።
የክልሉ የባህል፣ቅርስና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ አቶ ተወለዳ አብዶሽ፤ ከ130 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥና የውጭ አገራት ቱሪስቶች የክልሉን የቱሪዝም ሃብቶች መጎብኘታቸውን ገልጸዋል።
ከእነዚህ መካከል 123 ሺህ የሀገር ውስጥ ሲሆኑ ቀሪዎቹ የተለያዩ አገራት ቱሪስቶች መሆናቸውን አንስተው በዚህም 14 ሚሊዮን ብር ገቢ መገኘቱን ተናግረዋል።
ይህም ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር የ30 በመቶ እድገት ማሳየቱን ገልጸው በክልሉ ቱሪዝም ጥሩ የሃብት ምንጭ እየሆነ መምጣቱንም ገልፀዋል።
በተለይም የኮሪደር ልማት ክንውኑ ከተማዋን ውብና ለቱሪስቶች ምቹ ያደረጋት መሆኑን ጠቅሰው ታሪካዊ መስህቦችና ሌሎች የክልሉ እምቅ የቱሪዝም ሃብቶች መሆናቸውንም ጠቁመዋል።
አሶሳ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ ከስልጠናው ያገኘነው እውቀት ወቅቱ የሚጠይቀውን ብቁ የህብረት ስራ ማህበራትን ለመፍጠር ያግዘናል ሲሉ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክ...
Apr 29, 2026
ባህርዳር ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡- የአማራ ክልል በቴክኖሎጂ የታገዘ የገቢ አሰባሰብ ስርአትን በመተግበር ረገድ የተገኘው ውጤት ልምድና ተሞክሮ የሚወሰድበት...
Apr 15, 2026
ሮቤ፣ ሚያዝያ 5/2018 (ኢዜአ)፦ የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የቴክኖሎጂና የፈጠራ ዝንባሌ ያላቸው ተማሪዎችን ለተሻለ ውጤት ማብቃት የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወ...
Apr 14, 2026
አዲስ አበባ፤ የካቲት 20/2017(ኢዜአ)፦ የስንዴ ልማት ስራዎችን ለማስፋት መንግስት በትኩረት እየሰራ ነው ሲሉ የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ ገ...
Feb 28, 2025