
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2017(ኢዜአ)፦ በአንጎላ አዘጋጅነት በተካሄደው የአፍሪካ አሜሪካ የቢዝነስ ጉባኤ ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲዋን የሚያጠናክር ውጤታማ ተሳትፎ ማድረጓን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ።
17ኛው የአፍሪካ አሜሪካ የቢዝነስ ጉባኤ በትናንትናው ዕለት ተጠናቋል።
ጉባኤው ኢትዮጵያ ከሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች ጋር የተሰናሰነውን የቢዝነስ ዲፕሎማሲዋን ያጠናከረችበት መሆኑን በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጄኔራል አምባሳደር ዘርይሁን አበበ ለኢዜአ ገልጸዋል።

በጉባኤው የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ ውጤታማ የሁለትዮሽ ውይይቶች ማድረጋቸውን ተናግረዋል።
ከአንጎላው ፕሬዝዳንትና ከወቅቱ የአፍሪካ ኅብረት ሊቀ-መንበር ጆ ሌሬንሶ፤ ከአሜሪካው ፕሬዝዳንት የአፍሪካ ከፍተኛ አማካሪ ማሳድ ቦሎስና የአፍሪካ ኮርፖሬት ካውንስል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሎሪ ሊዘር ጋር መወያየታቸውንም ጠቅሰዋል።
ከዋናው ጉባኤ ጎን ለጎን በነበሩ የተለያዩ መድረኮች ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴን ጨምሮ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ብሩክ ታዬ(ዶ/ር) እና በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ዘለቀ ተመስገን(ዶ/ር) በኩል ተሳትፎ በማድረግ የኢትዮጵያን አቋም ማንጸባረቅ ተችሏል ብለዋል።
በዚህም በተለይም ኢትዮጵያ ለኢንቨስትመንት ምቹ መሆኗን ያሳየችባቸው፣ የዘርፉን የፖሊሲ ማዕቀፍ ያስተዋወቀችበት፣ የአፍሪካና የአሜሪካ የቢዝነስ ትስስር ምን መምሰል እንዳለበት እይታዋን ያካፈለችባቸው መድረኮች መሆናቸውን ጠቅሰዋል።
በሌላ በኩል በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ እና በአሜሪካ ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ትብብር መካከል የተፈረመው የመግባቢያ ሥምምነትም ኢትዮጵያ በቱሪዝም ዘርፍ የጀመረቻቸውን ሰፋፊ ጥረቶች ይበልጥ የሚያጠናክር መሆኑን አብራርተዋል።
ሥምምነቱ ከሁለት መቶ ሚሊየን ዶላር በላይ የኢንቨስትመንት ካፒታል የያዘ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም ኢትዮጵያ የቱርዝም መሰረተ ልማት በማስፋፋትና መዳረሻ ቦታዎችን በማልማት ምቹ ለማድረግ የያዘችውን ውጥን የሚያግዝ መሆኑን አስረድተዋል።
በተጓዳኝም፤ በጉባኤው የተለያዩ የግንኙነት መረቦች መዘርጋታቸውንም አምባሳደሩ ጨምረው ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ልዑክ በዚህ ጉባኤ ላይ መሳተፉ ከሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ጋር በማሰናሰን ኢትዮጵያ ለቢዝነስ ዲፕሎማሲ የሰጠችውን ትኩረት የሚያሳይ መሆኑንም ገልጸዋል።
አምባሳደሩ አክለውም ጉባኤው የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ጥረቶች ለማጠናከር ዕድል የፈጠረ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ጉባኤው በዋናነት ለኢትዮጵያ ምርቶች ገበያ በማፈላለግ፣ ለዜጎች የሥራ ዕድል በማስፋትና፣ የኢንቨስትመንት መዳረሻዎችን በማፈላለግና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ለመሳብ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል።
የዘንድሮው የአፍሪካ-አሜሪካ የቢዝነስ ጉባኤ አሜሪካ በፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የአስተዳደር ዘመን አፍሪካን በተመለከተ የምትከተለው የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ ድጋፍን መሰረት ካደረገው ወደ ቢዝነስ ዲፕሎማሲ እንዲሸጋገር የተወሰነውን ውሳኔ ተከትሎ መካሄዱ ልዩ አድርጎታል።
ኢትዮጵያ 10ኛውን የአፍሪካ-አሜሪካ ጉባኤ ማዘጋጀቷ ይታወሳል።
ዱራሜ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ) ፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በግብርና ዘርፍ ያሉ ፀጋዎችን ለልማት በማዋል የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመሩ ሥ...
Jun 6, 2026
ደሎ መና፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የአርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስ የሚያግዙ ዘመናዊ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑ...
May 26, 2026
ጋቼኖ ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልልን የሰላም፣ የልማትና የመቻቻል ተምሳሌት ለማድረግ የህዝቡን አቅም አቀናጅቶ መጠቀም እንደሚገባ የክ...
May 21, 2026
አሶሳ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ ከስልጠናው ያገኘነው እውቀት ወቅቱ የሚጠይቀውን ብቁ የህብረት ስራ ማህበራትን ለመፍጠር ያግዘናል ሲሉ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክ...
Apr 29, 2026